“ለፋሲል ከነማ ደጋፊ ትልቅ ክብር አለኝ” ሽመክት ጉግሳ

አስቀድሞ ከፋሲል ከነማ ጋር ውሉን ለማደስ ከስምምነት ደርሶ በዛሬው ዕለት ደግሞ ለቀድሞ ክለቡ ወላይታ ድቻ የመስማማቱን ምክንያት ሽመክት ጉግሳ ይናገራል።

በሊጉ ከሚጠቀሱ ምርጥ የመስመር አጥቂዎች መካከል አንዱ የሆነው ሽመክት ለተጨማሪ ዓመት ከዐፄዎቹ ጋር ለመቆየት አስቀድሞ ተስማምቶ እንደነበረ ይታወቃል። ነገር ግን በዛሬ ዕለት ለቀድሞው ክለቡ ወላይታ ድቻ ለሁለት ዓመት ለመጫወት ቅድመ ስምምነት ፈፅሟል፡፡ ይህን ተከትሎ ለፋሲል ከነማ ለመጫወት ከተስማማ በኃላ ሀሳቡን ቀይሮ ለወላይታ ድቻ ለመጫወት የወሰነበትን ምክንያት ለሶከር ኢትዮጵያ ተናግሯል።

” እኔ ፋሲልን የምከዳ አይደለሁም። አስቀድሜ በተስማማሁት መሠረት ሊፈፀሙልኝ የሚገቡ ጉዳዮች ተግባራዊ እንዲያደርጉልኝ በተደጋጋሚ የክለቡ የሚመለከታቸውን አካላት ከአስራ አምስት ቀን በፊት አናግሬያቸው ነበር። ሆኖም መልስ ሊሰጡኝ አልቻሉም። ስለዚህ የራሴን ውሳኔ ወሰንኩ እንጂ የኔ ጥፋት የለም። በፋሲል በቆየሁባቸው ዓመታት ሁሉ አብረውኝ ለነበሩት ደጋፊዎች በሙሉ ትልቅ ክብር አለኝ። ሌሎች የጠየቁኝ ክለቦች ቢኖሩም ለቤተሰቤ ቅርብ ለመሆን በማሰብ ለወላይታ ድቻ ለመጫወት ተስማምቻለው።”

ሽመክት ከዚህ ቀደም በወላይታ ድቻ፣ በአየር ኃይል፣ በሀዋሳ ከተማ፣ በደደቢት እንዲሁም በፋሲል ከነማ መጫወቱ ይታወቃል።

© ሶከር ኢትዮጵያ


👉እጅዎን በተደጋጋሚ በሳሙና በአግባቡ በመታጠብ አልያም አልኮል እና ሳኒታይዘር በመጠቀም

👉ከሰዎች ጋር ንክኪ በማስወገድ

👉ከአላስፈላጊ እንቅስቃሴ በመገደብ፣ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ እና በቤት በመቆየት ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!