ቡልቻ ሹራ ሲዳማ ቡናን ተቀላቅሏል

ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር በስምምነት የተለያየው የመስመር አጥቂ ሲዳማ ቡናን መቀላቀሉ ተረጋግጧል።

በአሠልጣኝ ወንድማገኝ ተሾመ የሚመራው ሲዳማ ቡና በቀጣይ ዓመት ተጠናክሮ ለመምጣት በዝውውር መስኮቱ በስፋት እየተንቀሳቀሰ ይገኛል። አሁን ባገኘነው መረጃ መሠረት ደግሞ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ቀሪ የአንድ ዓመት ውል እያለው በስምምነት የተለያየውን የመስመር አጥቂ አስፈርሟል።

ቡድኑን የተቀላቀለው ተጫዋች ቡልቻ ሹራ ነው።
ከአዳማ ወጣት ቡድን የተገኘው ቡልቻ 2007 ላይ ወደ ዋናው ቡድን አድጎ እስከ 2012 ድረስ ከቆየ በኋላ ወደ ሰበታ ከተማ አምርቶ እንደነበር አይዘነጋም። ዘንድሮ ደግሞ ፈረሰኞቹን ተቀላቅሎ የሊጉን ዋንጫ ከፍ ማድረግ የቻለ ሲሆን ቀሪ የአንድ ዓመት ውል ቢኖረውም በስምምነት ተለያይቶ በሁለት ዓመት ውል መዳረሻውን ሲዳማ ቡና አድርጓል።