አምሳሉ ጥላሁን ላይ የቅጣት ውሳኔ ተላለፈ

የሊግ ካምፓኒው ዲሲፕሊን ኮሚቴ በፋሲል ከነማው የግራ መስመር ተከላካይ አምሳሉ ጥላሁን ላይ የቅጣት ውሳኔ አስተላልፏል።

ባሳለፍነው ሳምንት ዐፄዎቹ ዋንጫ በተረከቡበት የሀዋሳ ጨዋታ ወቅት አምሳሉ ጥላሁን በጉዳት የጨዋታው አካል ባይሆንም በክቡር ትሪቡን ተቀምጦ ጨዋታውን ሲከታተል ቆይቷል። ሆኖም በጨዋታው መገባደጃ ላይ ለሀዋሳ ከተማ የተሰጠውን ፍፁም ቅጣት ምት በመቃወም ከተቀመጠበት ሥፍራ በመመነሳት ከዕለቱ ዳኞች ጋር ግብግብ መፍጠሩ ይታወሳል። በዚህም የሊግ ካምፓኒው የዲሲፕሊን ኮሚቴ የጨዋታው ኮሚሽነር እና ዳኛው ያቀረቡትን ሪፖርት ከመረመረ በኃላ ሦስት ጨዋታ እንዲታገድ እና 3000 ብር እንዲከፍል ተወስኗል።

የ2013 ውድድር ሊጠናቀቅ የአንድ ሳምንት ዕድሜ የሚቀረው በመሆኑ አምሳሉ ጥላሁን በሚቀጥለው ዓመት ሁለት የመጀመርያ ሁለት ጨዋታዎች የሚያልፉት ይሆናል።