ሦስቱ የባህር ዳር ከተማ ተጫዋቾች ወደ ልምምድ ተመልሰዋል

ከደሞዝ ጋር በተያያዘ ልምምድ አቁመው የነበረው የባህር ዳር ከተማ ተጫዋቾች ዛሬ ከቡድኑ ጋር ልምምድ ሰርተዋል።

አራት መደበኛ የልምምድ መርሃ ግብሮች እና አንድ የነጥብ ጨዋታ (ከፋሲል ከነማ ጋር) ያመለጣቸው ሀሪስተን ሄሱ፣ አዳማ ሲሶኮ እና ማማዱ ሲዲቤ ቡድናቸው ትላንት ከጎንደር ወደ ባህር ዳር ከተመለሰ በኋላ ወደ ስብስቡ መቀላቀላቸው ተሰምቷል። እነኚህ የቡድኑ ወሳኝ ተጨዋቾች ከክለቡ የቦርድ አመራሮች ጋር ንግግር እንዳደረጉ እና በድርድር ልምምድ እንዲጀምሩ እንደተደረገም ተገልጿል።

በ7ኛ ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ መርሐ ግብር በሜዳቸው ኢትዮጵያ ቡናን ከነገ በስትያ የሚጋብዙት የጣና ሞገዶቹ በጨዋታው የሦስቱን ተጨዋቾች ግልጋሎት እንደሚያገኝ ተጠቁሟል።

© ሶከር ኢትዮጵያ