ሀዲያ ሆሳዕና ከአጥቂ መስመር ተጫዋቹ ጋር ተለያየ

ዘንድሮ ሀድያ ሆሳዕናን ተቀላቅሎ የነበረው መሐመድ ናስር የውል ጊዜ እየቀረው በስምምነት ከክለቡ ጋር ተለያይቷል።

በኢትዮጵያ እግር ኳስ ረጅም ቆይታን ካደረጉ አንጋፋ አጥቂዎች መካከል የሚጠቀሰው መሐመድ ሲዳማ ቡናን ከለቀቀ በኋላ በክረምቱ የዝውውር መስኮት ወደ ሀዲያ ሆሳዕና የአንድ ዓመት ውል በመፈረም መቀላቀሉ ይታወሳል። ሆኖም ተጫዋቹ በቋሚነት በክለቡ ለመሰለፉ ዕድል እየተሰጠኝ አይደለም በሚል ለክለቡ የልቀቁኝ ደብዳቤ ያስገባ ሲሆን ክለቡም ተቀብሎት በጋራ ስምምነት ተለያይተዋል፡፡

መሐመድ ከዚህ ቀደም ክለቡ ያለፍቃድ በልምምድ አልተገኘም በሚል ማሰታወቂያ ማውጣቱ የሚታወስ ነው። ክለቡ ከመሐመድ በፊትም ከሳምንታት በፊት ከሴራሊዮናዊው አጥቂ ሙሳ ካማራ ጋር በስምምነት መለያየቱ ይታወቃል።

መሐመድ ናስር በሊጉ ለኤሌክትሪክ፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ኢትዮጵያ መድን፣ መከላከያ፣ ፋሲል ከነማ፣ ሲዳማ ቡና፣ አዳማ ከተማ እና ጅማ አባ ቡናን ጨምሮ ለበርካታ ክለቦች በመጫወት ልምድ ያካበተ አጥቂ ነው።


© ሶከር ኢትዮጵያ