ስሑል ሽረዎች የአማካያቸውን ውል ለማራዘም እንቅስቃሴ እያደረጉ ይገኛሉ

ባለፈው ዓመት አጋማሽ ፋሲል ከነማን ለቆ ወደ ስሑል ሽረ በማምራት ከቡድኑ ጋር የተሳካ አንድ ዓመት ያሳለፈው ዩጋንዳዊው ያስር ሙገርዋ ከስሑል ሽረ ጋር ያለውን ውሉን ለማራዘም ከጫፍ ደርሷል።

ተጫዋቹ ባለፈው ሳምንት በግል የማሕበራዊ ትስስር ገፁ ላይ ወደ ዩጋንዳ ፕሪምየር ሊግ ሊመለስ እንደሚችል ፍንጭ የሚሰጥ ፅሁፍ መለጠፉን ተከትሎ ወደ ሀገሩ ይመለሳል ተብሎ ሲጠበቅ የነበረው ይህ አማካይ ውሉን ለማራዘም ወደ አዲስ አበባ አቅንቶ ሒደቶችን የጀመረ ሲሆን በቀጣይ ቀናትም ሒደቱ ሙሉ ለሙሉ ይጠናቀቃል ተብሎ ይጠበቃል። ተጫዋቹ ምንም እንኳ ከአዲስ አበባ የቀናት ቆይታ በኋላ ወደ ቡድኑ ቢቀላቀልም የአንድ ዓመት ውሉ በመጠናቀቁ ምክንያት ከነገው ጨዋታ ውጭ መሆኑ ተረጋግጧል።

በኢትዮጵያ ቆይታው ለቅዱስ ጊዮርጊስ እና ፋሲል ከነማ መጫወት የቻለው ያሳር ሙገርዋ ከዚህ በፊት ለኦርላንዶ ፓይሬትስ እና ለሀገሩ ብሄራዊ ቡድን መጫወቱ ይታወሳል።

© ሶከር ኢትዮጵያ