ቅዱስ ጊዮርጊስ አሰልጣኙን አሰናበተ?

የቅዱስ ጊዮርጊስ ቦርድ ዋና አሰልጣኝ ሰርዳን ዝቪጅኖቭ እና የአሰልጣኝ ቡድን አባላት ላይ የዕግድ ውሳኔ ማሳለፉ ተሰምቷል።

በሊጉ ካለፉት ሁለት ዓመታት አንፃር የተሻለ የውጤት ጎዳና ላይ ቢገኙም የክለቡ ደጋፊዎች ግን በተደጋጋሚ በሰርቪያዊው አሰልጣኝ ሰርዳን ዝቪጅኖቭ ላይ ደስተኛ አለመሆናቸውን ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ የክለቡ ደጋፊዎች በሚያሰሙት ተደጋጋሚ የተቃውሞ ድምፅ መረዳት ይቻላል፡፡

ከዚህ መነሻነት ሰሞኑን ቦርዱ ለውይይት እንደሚቀመጥ መዘገባችን የሚታወስ ሲሆን ዛሬ ባደረገው ውይይት ዋና አሰልጣኙ ለጊዜው ከሥራቸው በእግድ እንዲነሱ መወሰኑን ለማወቅ ተችሏል። ረዳት አሰልጣኝ በመሆን ለዓመታት ሲያገለግል የነበረው ዘሪሁን ሸንገታ እና የግብ ጠባቂ አሰልጣኙ ዩጋንዳዊው ኤሚ ንዲዚዬም መታገዳቸውን ሰምተናል፡፡

ነገ በ17ኛው ሳምንት የፕሪምየር ሊግ ጨዋታ ከሰበታ ከተማ ጋር በአዲስ አበባ ስታዲየም ጨዋታ ያለበት ቅዱስ ጊዮርጊስ በክለቡ ተጫዋቾች ሳላሀዲን ሰዒድ እና ጌታነህ ከበደ እንዲሁም በቀድሞው የክለቡ ተጫዋቾች እየተመራ ጨዋታውን እንደሚያደርግ፤ አስቻለው ታመነም ቡድኑን በአምበልነት እንዲመራ ስለመመረጡ ከክለቡ ቅርበት ካላቸው ሰዎች አረጋግጠናል፡፡

ክለቡ እስካሁን በጉዳዩ ዙርያ ይፋ ያደረገው መረጃ የሌለ ሲሆን አዳዲስ እና ይፋ የሚወጡ መረጃዎችን ተከታትለን የምናቀርብ ይሆናል።

©ሶከር ኢትዮጵያ