የቅዱስ ጊዮርጊሱ ተከላካይ ለትውልድ ከተማው ድጋፍን አድርጓል

አብዱልከሪም መሐመድ ለትውልድ ከተማው ወንዶ ገነት ማኅበረሰብ ከፍተኛ ወጪ በማውጣት ድጋፍ አድርጓል፡፡

የቅዱስ ጊዮርጊሱ የተከላካይ ስፍራ ተጫዋች አብዱልከሪም መሐመድ በግሉ ሩብ ሚሊዮን ብር ወጪን በማውጣት በትውልድ ከተማው ወንዶ ገነት የፈሳሽ ሳሙና ማምረቻን አቋቁሞ ከነማሽኑ፣ ባለሙያዎች እና ግብአቶች ለከተማው እና ለወረዳው ህዝብ በነፃ እንዲከፋፈል በዛሬው ዕለት ያስረከበ ሲሆን የሚያመርቱ ባለሙያዎችን በመቅጠር ይህን በሽታ ከሀገራችን እንዲጠፋ የራሱን ድርሻ መወጣት ጀምሯል፡፡ ተጫዋቹ ከዚህም በተጨማሪ የንፅህና መጠበቂያ ሳኒታይዘሮች፣ በከተማው በየቦታው የሚቀመጡ ለእጅ መታጠቢያ የሚሆኑ በርካታ በርሜሎችን ለከተማው አስተዳደር አስረክቧል፡፡

የውሀ ዕጥረት እና በከተማው ማኅበረሰብ ዘንድ እየተስተዋለ በሚገኘው ቸልተኝተንት ምክንያት የሚፈለገውን ያህል ጥንቃቄ እየታየ የማይገኝ ሲሆን ህብረተሰቡም የዚህን በሽታ አስከፊነት በቶሎ ተረድቶ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ሶከር ኢትዮጵያ በስፍራው ተገኝታ ከተጫዋቾቹ ጋር ባደረገችው ቆይታ ተናግሯል፡፡ ተጫዋቹ ከነገ ጀምሮ በከተማዋ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስራዎችን ቲሸርቶችን በማሳተም እና ቤት ለቤትም ኅብረተሰቡን ለማስተማር ፕሮግራም መያዙን ገልጾ ለከተማው ጤና ተቋምም አስፈላጊ የህክምና ቁሳቁሶችን እንደሚያበረክት ተናግሯል።

👉እጅዎን በተደጋጋሚ በሳሙና በአግባቡ በመታጠብ አልያም አልኮል እና ሳኒታይዘር በመጠቀም

👉ከሰዎች ጋር ንክኪ በማስወገድ

👉ከአላስፈላጊ እንቅስቃሴ በመገደብ፣ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ እና በቤት በመቆየት ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!


© ሶከር ኢትዮጵያ