የአሰልጣኞች አስተያየት | ቅዱስ ጊዮርጊስ 0-1 ሀዲያ ሆሳዕና

ሀዲያ ሆሳዕና በሄኖክ አርፊጮ ብቸኛ የፍፁም ቅጣት ግብ ከረታበት ጨዋታ መጠናቀቅ በኃላ የሁለቱ ቡድኖች አሰልጣኞች ተከታዩን ሀሳብ ሰጥተዋል።

ኢያሱ መርሐፅድቅ – ሀዲያ ሆሳዕና 

ስለተከሉት ጥብቅ መከላከል 

“ስለመራን ብቻ ሳይሆን ስንጀምርም ጀምሮ ተከላክለን ለማጥቃት ነበር ያሰብነው ከግቧ በኃላ ያንን ሂደት ነበር አጠናክረን የቀጠልነው።”

በጨዋታው ከወጣት ተጫዋቾቹ የጠበቁትን ስለማግኘታቸው 

“ባለፈውም እንዳልኩት ነው ከጠበቅነው በላይ ነው ፤ ለእኔ አሁንም ከወጣት የመጡም ሆነ የነበሩት ተጫዋቾች እኩል ናቸው።በልምምድ ላይ ካሳዮን ጥሩ ነገር አንፃር በዛሬው ጨዋታ አምስት ተጫዋቾችን ተጠቅመናል ፤ ልጆቹ ላይ ሀላፊነት መውሰድ ግድ ስለሆነ አድርገን ግን ከምንፈልገው በላይ አተኝተናል።”

ስለሁለተኝነት ፉክክሩ 

“ግን ከዛሬው ጨዋታ አንፃር ተስፋ አለን ፤ ዋናው ነገር ቀጣይነት ነው።ከሰበታ ጋር ያደረግነውን ጨዋታ ካየህ ጥሩ ነበርን ቀጣይነቱን ደግሞ ዛሬ አይተናል ፤ እኛ በዋነኝነት ጠንክረን የምንሰራው በቀጣይነት ውጤት ለማስመዝገብ ነው።”

“ይህ ውጤት እዚህ ባለነው አካላት ብቻ የመጣ አይደለም ፤ ለዋና አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ ምስጋና ማቅረብ እፈልጋለሁ እነዚህ ልጆች እንዲመጡም ምክረ ሀሳብ ያቀረበው እሱ ነበር ከመጡ በኃላም ከዚህ እስኪሄድ ብዙ ስራዎችን ሰርቷል በዚህም የዛሬው ውጤት የእሱም ውጤት ነው።”

ፍራንክ ናታል – ቅዱስ ጊዮርጊስ 

ስለጨዋታው 

“በውጤቱ በጣም አዝኛለሁ ጨዋታውን በጥሩ መልኩ ነበር የጀመርነው በትኩረት ማጣት ተደጋጋሚ ኳሶችን እናጣ ነበር ግለሰባዊ ስህተቶች ዋጋ አስከፍለውናል በሂደት ያንን ለማረም በተለይ በሁለተኛው አጋማሽ ጥሩ ምላሽ ሰጥተናል ብዬ አስባለሁ በጥቅሉ ግን በቂ አልነበረም።”

በመከላከል ረገድ ቡድኑ እየተከተለው የሚገኘው ስልት ውጤታማ ነው ብለው የሚያስብ ከሆነ 

“ወደ ኃላ ተመልሰን ጨዋታዎችን ስንመለከት ግለሰባዊ ስህተቶች ዋጋ አስከፍለውናል ፤ ኳሱን የምንቆጣርበት እና ወደ ማጥቃት የምንሄድበት ሂደት ከፍ ያለ ነው ነገርግን በመከላከሉ ረገድ ግለሰባዊ ስህተቶች የምተሰራ ከሆነ ከባድ ነው።”

ሁለተኝነትን ይዘው ለማጠናቀቅ ስላላቸው እድል 

“አሁንም ተስፋ አለን ግን ከባድ ነው ፤ እንደምታዩት ሁሉም ቡድኖች ነጥብ እየጣሉ ነው ስለዚህ በቀሪ ጨዋታዎች እንታገላለን።”