“ቅዱስ ጊዮርጊስ ከቀጣቸው ተጫዋቾች ጋር በግል እየተገናኘን ነው” – ውበቱ አባተ

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ዋና አሠልጣኝ ውበቱ አባተ በቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ ቅጣት የተጣለባቸው ተጫዋቾችን በተመለከተ ለተጠየቁት ጥያቄ ሀሳብ ሰጥተዋል።

በአሁኑ ሰዓት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የአፍሪካ ዋንጫ የማጣሪያ ጨዋታዎች ጉዞን በተመለከተ የፓናል ውይይት በኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል እየተደረገ ይገኛል። ከረፋድ ጀምሮ እየተደረገ ባለው የውይይት መድረክ ላይ የተነሱ ዝርዝር ጉዳዮችን ከቆይታ በኋላ ይዘን የምንመለስ ሲሆን በመድረኩ ላይ በቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ክለብ የተቀጡ የብሔራዊ ቡድን ተጫዋቾችን በተመለከተ ለተነሳው ጥያቄ አሠልጣኝ ውበቱ አባተ በዚህ መልኩ አጭር ምላሽ ሰጥተዋል። 

“ቅዱስ ጊዮርጊስ ከቀጣቸውን ተጫዋቾች ጋር በግል እየተገናኘን ነው። ተጫዋቾቹ በትክክል ለምን እንደተቀጡ ከክለባቸው ለማወቅ ጥያቄ ባቀርብም ጉዳዩን ሊያስረዳኝ የሚችል ሰው አላገኘሁም። እንደ አጋጣሚ ሆኖ አሁን ላይ የብሔራዊ ቡድን ጨዋታ የለም። ግን ቢኖር ተጫዋቾቹን የማኅበራዊ ቅጣት ቀጥተን ስብስቡን እንዲቀላቀሉ እናደርጋለን።”

ቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ክለብ ከሳምንታት በፊት የዲሲፕሊን ግድፈት ፈፅመዋል ያላቸውን ጌታነህ ከበደ፣ አስቻለው ታመነ፣ ጋዲሳ መብራቴ እና ሙሉዓለም መስፍን የእግድ ቅጣት ማስተላለፉ ይታወቃል።

© ሶከር ኢትዮጵያ