የአሠልጣኞች አስተያየት | አዳማ ከተማ 2-1 ሀዋሳ ከተማ

የሳምንቱ የመጨረሻ ጨዋታ በአዳማ አሸናፊነት ከተጠናቀቀ በኋላ የሁለቱ ቡድኖች አሰልጣኞች አስተያየታቸውን ለሱፐር ስፖርት ሰጥተዋል።

ዘርዓይ ሙሉ – አዳማ ከተማ

ድሉ የዘገየ ስለመሆኑ

እስካሁን የምናደርገው እንቅስቃሴ ጥሩ ነበር። ለጎል እንቀርብ ነበር፤ ድል ያሳካነው ግን ዛሬ ነው። በእንቅስቃሴ ደረጃ የወረደ ቡድን አንመስልም ነበር። በራስ መተማመን ነበር ኳሱን ይዘው ሲጫወቱ የነበረው። ያለው ነገር ጥሩ ነው። ጊዜ ቢኖረን ጥሩ ነበር። ዞሮ ዞሮ የቀሩትን ጨዋታዎች በዚህ መንገድ ለመጨረስ ተዘጋጅተን እንመጣለን።

የውጪ ዜጎችን ስላለመጠቀሙ

ዛሬ ማጥቃት ነበር የፈለግነው። ለዛ ነው ያላስገባኋቸው። የውጪዎቹ መከላከል ላይ ጥሩ ናቸው። ከዚህ በፊት የነበሩት ጨዋታዎች በጥንቃቄ መደረግ የነበረባቸው ስለሆኑ እጠቀምባቸወሰ ነበር። ዛሬ ደግሞ ግዴታ ሦስት ነጥቡ ስለሚያስፈልገን በሀገር ውስጥ ተጫዋቾች በፈጣን እንቅስቃሴ ለመጫወት ነበር ያሰብነው። እሱም ተሳክቷል።

ስለ አብዲሳ ጀማል

አብዲሳ ጥሩ እና ወጣት አጥቂ ነው። ወደፊት ብዙ መሥራት የሚችል ታታሪ ተጫዋች ነው። ያለውን የሚሰጥ ተጫዋች ነው። ወደ ፊት ጥሩ ቦታ ይደርሳል ብዬ ነው የማስበው።

ሙሉጌታ ምኅረት – ሀዋሳ ከተማ

ስለ ጨዋታው

ጨዋታው ጠንካራ እንደሚሆን ጠብቀን ነበር። ሜዳ ላይ ያየነውም ነገር ከባድ ነበር። በዚህም ተሸንፈናል። ሽንፈቱን ተቀብለናል።

ወጣቶችን ስለመጠቀም

ዘንድሮ ከምደሰትባቸው ነገሮች መካከል ትልቁ ወጣቶችን መጠቀማችን ነው። ዓመቱን ስንጀምርም በወጣቶች የተሻለ ጠንካራ ቡድን ለመስራት አስበን ነበር። ይህም ስኬታማ ነው። ይህን ስታይ ያስደስታል።

ደረጃቸውን ከፍ የማድረግ እድላቸውን ስለማምከናቸው

አሁንም ውድድሩ እስከሚያልቅ ድረስ ስሜታችን ተመሳሳይ ነው የሚሆቸው። እያንዳንዱ ጨዋታን ትኩረት ሰጥተን በማሸነፍ ተፎካካሪ መሆን ነው አላማችን። ይህ ስሜት ይቀጥላል።

© ሶከር ኢትዮጵያ