አርባምንጭ ከተማ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐግብር ሊያከናውን ነው

የከፍተኛ ሊግ የምድብ ሐ ሻምፒዮን በመሆን ወደ ቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ ያደገው አርባምንጭ ከተማ ራሱን በገቢ ለማጠናከር ሁለት መርሐግብሮችን አዘጋጅቷል፡፡

አስቀድሞ የአሰልጣኝ መሳይ ተፈሪን ኮንትራት በማደስ በዛሬው ዕለት ደግሞ ሦስት አዳዲስ እንዲሁም አስር ነባር ተጫዋቾችን ያስፈረመው ክለቡ የፋይናንስ አቅሙን ለማጠናከር በያዝነው ወር ሁለት የገቢ ማሰባሰቢያ መርሀግብር እንዳዘጋጀ ሶከር ኢትዮጵያ ከክለቡ ያገኘችው መረጃ ይጠቁማል፡፡

በዚህም ሐምሌ 17 ላይ የተለያዩ ፕሮግራሞችን ያዘለ የገቢ ማሰባሰብ ፕሮግራምን ያዘጋጀ ሲሆን ሐምሌ 24 ደግሞ “ለአርባምንጭ ከተማ እሮጣለሁ” በሚል መሪ ቃል የጎዳና ሩጫ አዘጋጅቷል። ይህ ክለቡ ከመንግሥት ከሚያገኘው በጀት ተጨማሪ ገቢ ማግኘት እንዲችል ታልሞ እንደተዘጋጀም የክለቡ ሥራ አስኪያጅ አቶ ስንታየው ንገሤ ነግረውናል፡፡