ኬንያ ባህር ዳር የገባች ሁለተኛዋ ሀገር ሆናለች

ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን በመቀጠል የሴካፋ ውድድር ወደሚደረግበት ባህር ዳር ከተማ ያቀናችው ሁለተኛ ሀገር ኬንያ ሆናለች።

በአሠልጣኝ ስታንሊ ኦኩምቢ የሚመራው የኬንያ ከ23 ዓመት በታች ብሔራዊ ቡድን ለሴካፋ ውድድር ኢትዮጵያ መድረሱ ታውቋል። በምድብ ሦስት ከደቡብ ሱዳን እና ጂቡቲ ጋር የተደለደለው ብሔራዊ ቡድኑም በትናንትናው ዕለት የመጨረሻ ልምምዱን በሀገሩ ከሰራ በኋላ ረፋድ ላይ ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት በረራ ጀምሯል። ከሁለት ሰዓት በፊት ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ የደረሰው ልዑካን ቡድኑም ለደቂቃ እዛው አየር ማረፊያ ከቆየ በኋላ በተያያዥ በረራ ወደ ባህር ዳር አምርቷል።

ብሔራዊ ቡድኑ ከደቂቃዎች በፊት ባህር ዳር አየር ማረፊያ ሲደርስም በትናንትናው ዕለት ወደ ባህር ዳር ባመራው ሎካል ኦርጋናይዚንግ ኮሚቴ አቀባበል እንደተደረገለት ለማወቅ ችለናል። ቡድኑም ማረፊያውን በቤን ማስ ሆቴል እንደሚያደርግ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።