የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የደጋፊዎች ማሊያ ጉዳይ…?

የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ኢሳይያስ ጂራ የብሔራዊ ቡድኑ ደጋፊዎች ማሊያን በተመለከተ ገለፃ አድርገዋል።

የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ከወራት በፊት የብሔራዊ ቡድኖቹን ትጥቅ ከሚያቀርበው አምብሮ ጋር ስምምነቱን ማራዘሙ ይታወቃል። ለቡድኖቹ ከሚቀርበው የትጥቅ ስምምነት ጎን ለጎን ፌዴሬሽኑ የደጋፊዎችን መለያ ራሱ አስመጥቶ ለማከፋፈል መወሰኑ ሲገለፅ ነበር። ይህንን ተከትሎ ጉዳዩ ምን ደረጃ ላይ ደረሰ የሚለውን ጥያቄ የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ኢሳያስ ጂራ መልስ ሰጥተውበታል።

“የደጋፊዎች ማሊያን በተመለከተ ፌዴሬሽኑ ራሱ ለማስመጣት ወስኗል። ውሳኔውንም ተከትሎ ሥራዎች እየተሰሩ ይገኛሉ። በዚህም በዓመት 12,500 ማሊያ ለመግዛት ተስማምተናል። ማሊያውም ቱርክ ሀገር ተመርቶ አልቋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ የሚመጣውን ማሊያ እንዴት እናሰራጫለን የሚለው ጉዳይ የአመራር ውሳኔ የሚፈልግ ነው። ወይ ራሳችን ሱቅ ከፍተን እናከፋፍላለን አልያም በኤጀንት ማሊያዎቹ እንዲሸጡ እናደርጋለን። ይህ የግል አስተሳሰቤ ነው። ግን በአጠቃላይ በአመራር ደረጃ በሚወሰን ውሳኔ ማሊያውን ለደጋፊዎች የምናሰራጭ ይሆናል። ግን የውጪ ምንዛሬ ጉዳይ ሂደቱ እንዲጓተት አድርጎት ነበር።”