ሀዋሳ ከተማ ካሜሩናዊ አጥቂ አስፈርሟል

ካሜሩናዊው የፊት መስመር ተጫዋች ወደ ሀዋሳ ከተማ አምርቷል።

በአሰልጣኝ ዘርዓይ ሙሉ እየተመሩ አዳዲስ ተጫዋቾች እያስፈረሙ እንዲሁም ደግሞ የነባሮችን ውል በማደስ ያለፉትን ጊዜያት የሰነበቱት ሀዋሳ ከተማዎች አሁን ደግሞ ካሜሩናዊው የአጥቂ ስፍራ ተጫዋች ኤሚ ጄይካ ጋሲሶውን ማስፈረማቸውን ሶከር ኢትዮጵያ ያገኘችው መረጃ ይጠቁማል፡፡

1 ሜትር ከ85 ሴንቲ ሜትር የሚረዝመው ኤሚ ሌስ አስተርስ ለተባለ የሀገሩ ክለብ ከተጫወተ በኋላ ለደቡብ ኮሪያው ክለብ ኢችኦን ሲትዝን በመጫወት የእግር ኳስ ህይወቱን መግፋትን ቀጥሏል፡፡ በመቀጠል ወደ ቬትናም ካመራም በኋላ ኤስ ኤች ቢ ዳ ናንግ ለተባለ ቡድን እንዲሁም ደግሞ እስከ ዘንድሮ የውድድር ዓመት አጋማሽ ድረስ ደግሞ ታንች ሆአ ለተባለ ክለብ ግልጋሎት በመስጠት ቆይቷል፡፡ ፈጣን እንደሆነ እና በሁለቱም እግሮቹ መጫወት እንደሚችል የሚነገርለት ይህ ተጫዋች ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት ሀዋሳ ከተማን እንደሚቀላቀል እርግጥ ሆኗል፡፡