ድሬዳዋ የመስመር አጥቂ አስፈርሟል

በሀዋሳ ቅድመ ዝግጅቱን እያደረገ የሚገኘው ድሬዳዋ ከተማ የመስመር አጥቂውን የግሉ አድርጓል።

በአሰልጣኝ ዘማርያም የሚመሩት ድሬዳዋ ከተማዎች ወደ ዝውውር ገብያው ከገቡ በኃላ በርከት ያሉ ተጫዋቾችን ያስፈረሙ ሲሆን አሁን ደግሞ የመጨረሻ ፈራሚ እንደሆነ የተነገረለትን አብዱራህማን ሙባረክ አስፈርመዋል።

በኢትዮጵያ ቡና ተስፋ ቡድን የእግርኳስ ህይወቱን ጅማሬ ያደረገው አብዱራህማን በመቀጠል በአዲስ አበባ ከተማ እና ፋሲል ከነማ የተጫወተ ሲሆን በተጠናቀቀው የውድድር ዘመን እስከ አጋማሹ ድረስ በወልቂጤ ከተማ ቆይታ ማድረጉ ይታወሳል።

ለሁለት ዓመት ለድሬደዋ ከተማ ለመጫወት ፊርማውን ያኖረው አብዱራህማን በፋሲል ካሰለጠኑት ዘማርያም ጋር ዳግም የሚገናኝ ይሆናል።

በሌላ ዜና የቡድኑ ነባር ተጫዋች እና አንበሉ ያሬድ ዘውድነህ ውል በቅርቡ ክለቡ ያራዝማል ተብሎ ይጠበቃል።