ሀዋሳ ከተማ በፌዴሬሽኑ የተወሰነበትን ውሳኔ ተፈፃሚ አደረገ

ገብረመስቀል ዱባለ በ2012 ከሀዋሳ ጋር ውል እያለው በመሰናበቱ ለፌዴሬሽኑ ያቀረበውን አቤቱታ ተከትሎ የተወሰነለት ወሳኔ ተፈፃሚ ሆኖለታል፡፡

ከሀዋሳ ከተማ ታዳጊ ቡድን ከተገኘ በኃላ በስልጤ ወራቤ ጥሩ እንቅስቃሴ በማሳየቱ ወደ ልጅነት ክለቡ በ2011 ለሁለት አመት ፈርሞ የነበረው አጥቂው ገብረመስቀል ዱባለ ዓምና ጉዳት በማስተናገዱ ለመቀነስ ይገደዳል፡፡ ሆኖም ተጫዋቹ የአስራ አንድ ወር ውል እያለው መሰናበቱን በመግለፅ ክስ ካቀረበ በኃላ የፌዴሬሽኑ የዲሲፕሊን ኮሚቴ በክለቡ ላይ ሙሉ በሙሉ ደመወዝ እስኪከፍል የእግድ ውሳኔ መተላለተፉ ይታወሳል። ክለቡም ይህ ጉዳይ በወቅቱ በነበሩ አመራሮች የተፈጠረ ስህተት የነበረ በመሆኑ አምኖ ለተጫዋቾቹ የሚገባውን የአስራ አንድ ወር ደመወዝን በዛሬው ዕለት መክፈሉን የክለቡ ዋና ፀሀፊ አቶ አንዱአለም አረጋ ለሶከር ኢትዮጵያ ገልፀዋል፡፡ ተጫዋቹም ያቀረበው ቅሬታ ተፈፃሚ በመሆኑ ደስተኛ መሆኑን የገለፀ ሲሆን የፌዴሬሽኑ ፅህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ባህሩ ጥላሁንም ሀዋሳ ከተማ ከሌሎች ክለቦች በተሻለ ፈጥኖ እልባት መስጠቱ ለሌሎች አርዓያ እንደሆነ ለክለቡ በላኩት መልዕክት ገልጸዋል፡፡

© ሶከር ኢትዮጵያ


👉ሳንዘናጋ አስፈላጊውን ጥንቃቄ በማድረግ ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!