የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ማጠቃለያ ውድድር በሀዋሳ መካሄዱን ቀጥሎ የምድብ ጨዋታዎች ፍፃሜያቸውን አግኝተዋል፡፡
08:00 ላይ ደደቢት ቅዱስ ጊዮርጊስን ገጥሞ 3-1 በማሸነፍ በ100% የማሸነፍ ሪኮርድ ወደ ግማሽ ፍፃመሜው ተቀላቅሏል፡፡
የደደቢትን የድል ግቦች ልማደኛዋ ሎዛ አበራ (2) እና ነህምያ ሲያስቆጥሩ የፈረሰኞቹን ብቸኛ ግብ ቱቱ በላይ ከመረብ አሳርፋለች፡፡
ውጤቱን ተከትሎ ደደቢት በሙሉ 12 ነጥብ ወደ ግማሽ ፍፃሜ ሲያልፍ በማሸነፍ ላይ ብቻ የተመሰረተ እድል ይዞ የገባው ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ግማሽ ፍጻሜ ሳያልፍ ቀርቷል፡፡ መከላከያ ደደቢትን ተከትሎ ያለፈ ቡድን ሆኗል፡፡
10:00 ላይ መውደቃቸውን ያረጋገጡት ሲዳማ ቡና እና አርባምንጭ ከተማ ባደረጉት ጨዋታ ሲዳማ 4-1 አሸንፏል፡፡ ሰአዳ ኡስማን ሶስት ግቦች አስቆጥራ ሐት-ትሪክ ስትሰራ አስራት አለሙ ቀሪዋን ግብ አስቆጥራለች፡፡ የአርባምንጭን ብቸኛ ግብ መሰረት ማቲዮስ አስቆጥራለች፡፡
የግማሽ ፍፃሜ ጨዋታዎች በመጪው ሀሙስ በአዲሱ የሀዋሳ ኢንተርናሽናል ስታድየም ሲካሄዱ 08:00 ላይ ደደቢት ከ ዳሽን ቢራ ፤ 10:00 ላይ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከ መከላከያ ይፋለማሉ፡፡
የከፍተኛ ግብ አግቢነቱን ሎዛ አበራ በ8 ግቦች ስትመራ ሽታዬ ሲሳይ በ5 ትከተላለች፡፡