የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ በደደቢት ቻምፒዮንነት ዛሬ ፍጻሜውን አግኝቷል፡፡ ንግድ ባንክ ከ3 ተከታታይ አመታት ድል በኋላ ንግስናውን ለደደቢት ሲያስረክብ መከላከያ በ3ኛ ደረጃ ውድድሩን አጠናቋል፡፡
ረፋድ 05:00 ላይ በተደረገው የደረጃ ጨዋታ የማጠቃለያ ውድድሩ ድምቀት የነበረውና በማራኪ እንቅስቃሴ የብዙዎችን መሳብ የቻለው መከላከያ ዳሽን ቢራን 3-0 በማሸነፍ በ3ኛ ደረጃነት ውድድሩን ፈፅሟል፡፡
የመከላክያን የድል ጎል ከእረፍት መልስ ምስራች ላቀው (2) እና ፍቅርተ ብርሀኑ ሲያስቆጥሩ በየጨዋታው ግሩም እንቅስቃሴ እያደረገች ለቡድኑ ውጤት ማማር ከፍተኛ ሚና የነበራት የመከላከያዋ እመቤት አዲሱ ከተመልካቹ ከፍተኛ ሙገሳ አትርፋለች፡፡
09:00 ላይ በተጀመረው የፍጻሜ ጨዋታ ደደቢትኢትዮጵያ ንግድ ባንክን 2-0 በማሸነፍ ከ3 አመታት በኋላ የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ቻምፒዮን ሆኗል፡፡
በመጀመርያው አጋማሽ የመጀመሪያ 25 ደቂቃዎች ንግድ ባንኮች የእንቅስቃሴ ብልጫ ቢኖራቸውም ድንቅ አቋም ላይ የምትገኘው ሊያ ሽብሩን መረብ መድፈር አልቻሉም፡፡ በአንጻሩ ቀስ በቀስ ኸደ ጨዋታው መግባት የቻሉት ደደቢቶች በሎዛ አበራ የ32ኛ ደቂቃ ግብ የመጀመርያውን አጋማሽ በመሪነት ማጠናቀቅ ችለዋል፡፡
በሁለተኛው አጋማሽ ከመጀመርያው በተቃራኒ ደደቢት ተደጋጋሚ የግብ እድሎችን መፍጠር የቻሉ ቢሆንም ሎዛ አበራ ሳትጠቀምባቸው ቀርታለች፡፡ በ56ኛው ደቂቃ የተሰጠውን የፍጹም ቅጣት ምት ሎዛ አበራ በአግባቡ ተጠቅማ የደደቢትን መሪነት ማስፋት ችላለች፡፡ ይህች ግብ ለሎዛ አበራ በማጠቃለያው 10ኛ ግብ ሆና ተመዝግባለች፡፡
ንግድ ባንኮች ወደ ጨዋታው የሚመልሳቸውን ግብ ለማግኘት ያደረጓቸው ተደጋጋሚ ጥረቶች በሊያ ሽብሩ ሲከሽፉ በጨዋታው የመጨረሻ ደቂቃ የደደቢቷ አማካይ አልፊያ ጃርሶ ከዳኞች ጋር በፈጠረቸው እሰጥ እገባ በቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብታለች፡፡
ከጨዋታው ፍጻሜ በኀላ የሽልማት ስነ ስርአት የተካሄደ ሲሆን ከሌሎች አመታት በተለየ ዘንድሮ በዞን ውድድር በቻምፒዮንነት እና ከፍተኛ ግብ አግቢነት ላጠናቀቁ ሽልማት ተበርክቷል፡፡
የኢትዮጵያ ንግድ ባንኳ ሽታዬ ሲሳይ በኮከብ ተጫዋችነት ስትሸለም ሎዛ አበራ በ10 ግቦች ከፍተኛ ግብ አግቢ ሆና ተሸልማለች፡፡
የሽልማቶች ዝርዝር ይህንን ይመስላል፡-
1ኛ ደረጃ – ደደቢት
የወርቅ ሜዳልያ ፣ ዋንጫ እና 100,000 ብር
2ኛ ደረጃ – ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
የብር ሜዳልያ እና 75,000 ብር
3ኛ ደረጃ – መከላከያ
የነሀስ ሜዳልያ እና 50,000 ብር
የስፖርታዊ ጨዋነት ዋንጫ – መከላከያ
ኮከብ አሰልጣኝ – ፍሬው ኃ/ማርያም (ደደቢት)
-15,000 ብር እና ዋንጫ
ኮከብ ተጫዋች – ሽታዬ ሲሳይ (ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ)
– 15,000 ብር እና ዋንጫ
ከፍተኛ ግብ አግቢ – ሎዛ አበራ (10 ግቦች)
– 15,000 ብር እና ዋንጫ
ኮከብ ግብ ጠባቂ – ሊያ ሽብሩ (ደደቢት)
-10,000 ብር እና ዋንጫ
የዞን ከፍተኛ ግብ አግቢዎች
በየዞኑ ኮከብ ጎል አስቆጣሪ የሆኑት ሎዛ ፣ አይናለም አሳምነው እና ተራማጅ ተስፋዬ እያንዳንዳቸው የ5000 ብር ተሸላሚ ሆነዋል፡፡
የዞን አሸናፊዎች
የማከላዊ-ሰሜን ዞን አሸናፊ – ደደቢት የደቡብ ዞን አሸናፊ – ሀዋሳ ከተማ የዋንጫ ተሸላሚ ሆነዋል፡፡
የአመቱ ኮከብ ዳኞች
ዋና ዳኛ – ሊዲያ ታፈሰ – 10,000 ብር እና ዋንጫ
ረዳት ዳኛ – ወጋየሁ ዘውዴ – 8,000 ብር እና ዋንጫ