የኢትዮጵያ ከ17 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ የማጠቃለያ ውድድር 2ኛ ቀን ጨዋታዎች ዛሬ ሲካሄዱ ሀዋሳ ከተማ እና ሐረር ሲቲ ተጋጣሚዎቻቸውን በመርታት የምድብ ጨዋታቸውን በድል ጀምረዋል፡፡
08:00 ላይ የደቡብ-ምስራቅ ቻምፒዮን እና የጥሎ ማለፉ የፍጻሜ ተፋላሚ የሆነው ሀዋሳ ከተማ ቅዱስ ጊዮርጊስን 2-1 አሸንፎ ውድድሩን በድል ከፍቷል፡፡
እጅግ ጠንካራ ፉክክርና ማራኪ እንቅስቃሴ በታየበት የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ የሀዋሳን የድል ግቦች በዞኑ ግብ አዳኝነቱን ያስመሰከረው ወንድማገኝ ታደሰ እና ምንተስኖት ማቲዮስ ሲያስቆጥሩ የፈረሰኞቹን ብቸኛ ጎል እንደልቤ ደሴ አስቆጥሯል፡፡
በዚህ ጨዋታ ላይ የተጎዳ ተጨዋች ይዞ የሚወጣ የተሟላ ሰራተኛ አለመመደቡ ተመልካቹን ያስቆጣ ሲሆን የመጀመርያ እርዳታ ባለሙያ እና ሜዳ ላይ የሚገኝ ተጨዋች የተጎዳውን ተጫዋች ይዘው ለመውጣት ተገደዋል፡፡
10:00 ላይ ሐረር ሲቲ ከ አአ ከተማ ባደረጉት ጨዋታ ሐረር ሲቲ 1-0 አሸንፏል፡፡
በዞኑ ውድድረር በማራኪ እንቅስቃሴያቸው የአአ ስታድየም ተመልካችን መማረክ የቻሉት ሐረር ሲቲዎች የአዳማን ተመልካችን ቀልብ ለመግዛትም አልተቸገሩም፡፡የሐረርን የድል ጎል ከዕረፍት በፊት በፍፁም ቅጣት ምት ከመረብ ያሳረፈው ታዲዮስ አዱኛ ነው፡፡
የአዳማ አበበ ቢቂላ ስታድየም በሁለቱ ቀናት ልዩ ድባብ እና ስፖርታዊ መንፈስ እየታየባትሲሆን በዛሬው ውሎ በአዳማ ከተማ ስፖርት ክለብ የልብ ደጋፊነቱ የሚታወቀው “እሙጥሽ” በስቴዲዮም የተገኘውን የስፖርት ቤተሰብ ሲያዝናና ውሏል፡፡
ውድድሩ ነገ ሲቀጥል ከምድብ ለ 08:00 ላይ ደደቢት ከ አዳማ ከተማ ፤ 10:00 ላይ ወላይታ ድቻ ከ መከላከያ ጨዋታቸውን ያደርጋሉ፡፡ ከ17 አመት በታች ጨዋታዎች በፊት ደግሞ በከፍተኛ ሊጉ አማራ ውሃ ስራ ከ ኢትዮጵያ ውሃ ስፖርት 5:00 ላይ ይፋለማሉ፡፡