የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ 26ኛ ሳምንት ዛሬ በተደረጉ ጨዋታዎች ሲጀምር ጎንደር ላይ ኢትዮጵያ መድንን ያስተናገደው ፋሲል ከተማ 1-0 በማሸነፍ ለከርሞ ወደ ፕሪሚየር ሊግ ማደጉን አረጋግጧል፡፡
ፋሲል ከተማ ይህን ጨዋታ ካሸነፈ ወደ ፕሪሚየር ሊግ እንደሚያልፍ የሚያረጋግጥ በመሆኑ የክለቡ ደጋፊዎች ጨዋታው ከመጀመሩ ሰአታት በፊት የአፄ ፋሲለደስ ስታድየምን ከአፍ እስከ ገደፉ ሞልተው ጨዋታውን ቢጠባበቁም በጣለው ዝናብ ምክንያት ጨዋታው በ1 ሰአት ዘግይቶ 10፡00 ላይ ተጀምሯል፡፡
ፋሲል ከተማ 1-0 ባሸነፈበት ጨዋታ የፋሲል ከተማ ደጋፊን ከረጅም ጊዜ ተስፋ ወደ ከፍተኛ የደስታ ስሜት የለወጠችዋን የድል ግብ ከመረብ ያሳረፈው ይስሃቅ መኩሪያ ነው፡፡
ከ26 ጨዋታዎች 57 ነጥቦችን የሰበሰበው ፋሲል ከተማ በ2000 በኋላ ወደ ፕሪሚየር ሊጉ የተመለሰ ሲሆን በቀጣይ ሳምንት አርብ ወልድያ ከ ኢትዮጵያ ውሃ ስራ ጋር በሚያደርገው ጨዋታ ካሸነፈ ፋሲል ከተማን ተከትሎ ወደ ፕሪሚየር ሊጉ መመለሱን ያረጋግጣል፡፡
በአሁኑ ሰአት በጎንደር ከተማ በከፍተኛ የደስታ ድባብ እየተናጠች እንደሆነ ከስፍራው ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
በምድብ ለ ዛሬ በተደረገ አንድ ጨዋታ ፌዴራል ፖሊስ ሀላባ ከተማን 2-1 አሸንፏል፡፡