ከ2008 የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ወደ ፕሪሚየር ሊጉ ካደጉት 4 ክለቦች መካከል አዲስ አበባ ከተማ አንዱ ነው፡፡
በምድብ ለ 2ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው አአ ከተማ ከ2 ሳምንት በፊት ፌዴራል ፖሊስን 2-0 በማሸነፍ በተመሰረተ በ5ኛ አመቱ ወደ ፕሪሚየር ሊጉ ማደጉን አረጋግጧል፡፡
ለቡድኑ ማራኪ አጨዋወት እና ውጤታማነት ትልቁን ድርሻ የሚወስዱት አሰልጣኝ ስዩም ከበደ ለሶከር ኢትዮጵያ በሰጡት አስተያየት የውድድር ዘመኑ በፈተና የተሞላ እንደነበር ይገልጻሉ፡፡
‘’ወደ ክለቡ የተቀላቀልኩት ዘግይቼ እንደመሆኑ እና ከክለቡ የተረከብኩት 12 ተጨዋቾች ብቻ እንደመሆናቸው በአመቱ መጀመሪያ ላይ ብዙ ፈተናዎች ነበሩብኝ፡፡ ነገር ግን አዳዲስ ተጨዋቾችን አስፈርመን ውድድሩን ማከናወን ችለናል፡፡
” በአመቱ ውስጥ ያለው ውጣ ውረድ በጣም ከፍተኛ ቢሆንም ያሉኝ ተጨዋቾች ወጣት እና ፍላጎት ያላቸው ስለነበሩ ከኔ የጨዋታ ፍልስፍና ጋር ቶሎ ተዋህደውልኝ አመቱን በስኬት ጨርሰናል’’፡፡
አሰልጣኝ ስዩም የስኬታችን ምስጢር ነው ያሉትንም ያክላሉ፡፡
‘’ከምንም በላይ ቡድኑ ውስጥ ያሉትን ተጨዋቾች ስመርጥ በተቻለው አቅም ባለ ክህሎት ተጨዋቾችን ለማሰባሰብ ሞክሬያለው፡፡ ይህ ደግሞ እንደ እኔ አስተሳሰብ አንድ ቡድን ጨዋታ ማሸነፍ የሚችለው ኳሱን በደንብ ተቆጣጥሮ የተጋጣሚን ቡድን በልጦ መጫወት ሲችል ነው፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ የምንሰጣቸውን ልምምዶች የመቀበል አቅማቸው እጅግ ከፍተኛ ስለነበር ብሎም የያዝናቸው ተጨዋቾች በሜዳ ላይ ያላቸው በራስ የመተማመን ብቃት እጅግ እያደገ መሄዱ ፤ ከምንም በላይ ደግሞ እኔ እና ተጨዋቾቼ ተቀራርበን ስለምንሰራ ለውጤታችን ማማር ከፍተኛ አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡
“ቡድኑ በአጠካላይ ከቦርዱ እስከ ታች ድረስ ሁሉም በህብረት በመተጋገዝ እና በመተሳሰብ ስለምንሰራም ነው ለዚህ ስኬት የበቃነው’’ ብለዋል፡፡
አዲስ አበባ ከተማ አስቀድሞ ወደ ፕሪሚየር ሊጉ ማደግ ቢችልም እንደ ክለብ የሊጉ ልምድ የለውም ፤ አመዛኞቹ ተጫዋቾችም እንደዛው፡፡ አሰልጣኝ ስዩም ከበደም በሊጉ ለመፎካከር ተጨማሪ ተጫዋቾች እንደሚያስፈልጓቸው ያምናሉ፡፡
‘’በቀጣይ አመት አሁን ካሉን የተጨዋቾች ስብስብ የተሻሉ ተጨዋቾችን በማስፈረም በሚቀጥለው አመት የተሻለ ተፎካካሪ ቡድን ለመስራት ጥረቶችን እናደርጋለን፡፡ ቡድኑ በሚቀጥለው አመት ተፎካካሪ እንዲሆን ሁለት የአጥቂ አማካይ እና አጥቂ እንዲሁም የኃላ መስመራችንን ደግሞ ለማጠናከር አራት ተጨዋቾችን ከኬንያ እናመጣለን’’ የሚሉት አሰልጣኝ ስዩም ከሚመጡት ተጨዋቾች መካከል ለዋናው የኬንያ ብሄራዊ ቡድን የሚጫወቱ ተጨዋቾችም እንዳሉበት ተናግረዋል፡፡