ቀይ ቀበሮዎቹ በአፍሪካ ከ17 ዓመት በታች ዋንጫ ማጣርያ ወደ ተከታዩ ዙር ለማለፍ ግብፅን ድሬዳዋ ስታዲየም ላይ ይገጥማል፡፡
በመጀመርያው የካይሮ ጨዋታ ድንቅ አቋም ያሳዩት ጫላ ተሺታ፣ ሚኪያስ መኮንን እና ግብ ጠባቂው ኦኛ ኡሙኛ ስለ ጨዋታው እና ተያያዥ ጉዳዮች ለሶከር ኢትዮጵያ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
“ከልክ በላይ በራስ መተማመን የለብንም” ጫላ ተሺታ
ስለመጀመሪያው ጨዋታ
“በተለምዶ የሰሜን አፍሪካ ቡድኖችን መርታት ይከብዳል ይባላል፡፡ ነገር ግን ዋናው ነገር መስራት ነው፡፡ ብዙ ጊዜ ታዳጊ ላይ ከተሰራ ለውጥ ሊመጣ እንደሚችል ፍንጭ የሰጠ ውጤት ነው፡፡ አሰልጣኞቼ የሚሰጡኝን ልምምዶች በአግባቡ በመስራቴ ለማሸነፍ ያለኝ መነሳሳት በጨዋታው ጥሩ እንድቀሳቀስ አድርጎኛል፡፡”
ስለመልስ ጨዋታው
“ከልክ በላይ በራስ መተማመን የለብንም፡፡ ወደ ሜዳ ስንገባ 0-0 ሆነን ነው፡፡ 90 ደቂቃ ይቀራል ፤ የእግርኳስ ነገርም ባይታወቅም ጨዋታውን አሸንፈን ታሪካዊ ቡድን መሆን እንፈልጋለን፡፡”
“ሜዳችን ላይ እናሸንፋለን” ሚኪያስ መኮንን
ስለዝግጅት እና ጨዋታው
“ዝግጅት በጣም ጥሩ ነበር፡፡ በመልካም ሁኔታ ተዘጋጅተናል፡፡ በመልሱ ጨዋታ የመዘናጋት ነገር አይኖርም፡፡ ጨዋታው አላለቀም ገና ሰፊ 90 ደቂቃ ይቀራል፡፡ በደንብ ተጭነን ተጫውተን ሜዳችን ላይ እናሸንፋለን፡፡ ከእኔ ብቻ ሳይሆን ከሙሉ ቡድኑ ጥሩ ነገር ጠብቁ፡፡”
ግብፅ ላይ ስላስቆጠራት ግሩም ግብ (3 ተጫዋቾች እና ግብ ጠባቂውን አልፎ ነበር ያስቆጠረው)
“በጣም ደስ ይላል፡፡ አንደኛ ለክለብ ሳይሆን ለሃገር ነው ግብ ማስቆጠር የቻልኩት፡፡ ለሃገር ግብ ማስቆጠር በራሱ ደስታ ይሰጥሃል፡፡ ግቡም ጥሩ ስለነበር በጣም ደስ ብሎኛል፡፡”
“በእኛ እድሜ ጥሩ ነገር ለመስራት ነው አላማችን” ኦኛ ኡሙኛ
ስለመልስ ጨዋታ
“እኛ የምናስበው 0-0 ሆነን ወደ ሜዳ መግባታችንን ነው፡፡ ይህ እግርኳስ ነው 90 ደቂቃ አለ፡፡ እኛ ካይሮ ላይ የሰራነውን እነሱም እዚህ ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡ እኛም ዳግም እንደአዲስ እነሱን ለማሸነፍ ነው ወደ ሜዳ የምንገባው፡፡በእኛ እድሜ ጥሩ ነገር ለመስራት ነው አላማችን፡፡”
ስለግብ ጠባቂነት
“አባቴ ከኮንጎ ብራዛቪል ነው፡፡ የዘር ነገሩ ይመስለኛል በአካል ብቃቱ ጠንካራ እንድሆን ያስቻለኝ፡፡ ልምምዶችን በየቀኑ ስለምሰራ ያለህ ተስጥኦ ላይ ከጨመርክበት ጥሩ ደረጃ ትደርሳለህ፡፡ እግርኳስን የጀመርኩት ግብ ጠባቂ ሆኜ ነው፡፡ ከህፃንነቴ ጀምሮ ግብ ጠባቂዎች ስለምመለከት ነው ወደ ሙያው የተሳብኩት፡፡”