የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን ግብፅን በአጠቃላይ ውጤት 5-2 በማሸነፍ ወደ ቀጣዩ የማጣሪያ ዙር ማለፍ ችሏል፡፡ ከቀይ ቀበሮዎቹ 5 ግቦች መካከል ሶስት ግቦች ግብፅ ላይ ያስቆጠረው አቡበከር ነስሮ እና በጨዋታው ጥሩ ሲንቀሳቀስ የነበረው 2ኛ አምበሉ እሱባለው ጌታቸው ከጨዋታው መጠናቀቅ በኃላ ስለጨዋታው ለሶከር ኢትዮጵያ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
“ ህዝቡ በተሰፋ ማዳካስካር ይጠብቀን ” አቡበከር ነስሮ
ስለጨዋታው
“ጨዋታው ጥሩ ነበር፡፡ በሜዳችን ያደረግነው የመጀመሪያ ኢንተርናሽናል ግጥሚያ ስለነበር ተረጋግተን መጨዋት አልቻልንም ነበር፡፡ ይህም በመጀመሪያው አጋማሽ ኳስን ተቆጣጥሮ ለመጫወት እንቅፋት ሆኖብናል፡፡ ያም ሆኖ ጥረናል ግቦችንም አስቆጥረናል ስለዚህም ውጤቱ ጥሩ ነው፡፡ ግብ በማስቆጠሬም ደስ ብሎኛል፡፡”
ስለግብፅ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን
“ጫና ፈጥረው ይጫወታሉ፡፡ በነሱ ሜዳ የተሻለ እንቅስቃሴ ነበረን ዛሬ ግን የሜዳው አለመመቸት በጫዋታ የበለጠ ቡድን እንዳይኖር አድርጓል፡፡”
ስለቀጣይ ተጋጣሚ
“ከቡድን አጋሮቼ ጋር ሁሉም በተሰጠው ቦታ ላይ ጥሩ ስታ ሰርቶ ወደ አፍሪካው ዋንጫው ለማለፍ ነው ፍላጎታችን፡፡ እግርኳስ የሚሆነው አይታወቅም የቻልነውን አርገን እንወጣለን፡፡ ህዝቡም በተሰፋ ማዳካስካር ይጠብቀን፡፡”
ስለሃረር ሲቲ አሰልጣኝ እስማኤል አቡበከር
“አሰልጣኝ እስማኤል አቡበከር በጣም ጥሩ ሰው ነው፡፡ እኔ ገንዘብ በማይኖረኝ ሰዓት የትራንስፖርት ከራሱ ወጪ ይሰጠኝ ነበር፡፡ ጥሩ አሰልጣኝ ነው ለወደፊት በጣም ጥሩ ደረጃ እንደሚደርስ ተስፋ አደርጋለው፡፡”
“የተሻለ ውጤት አምጥተናል ብዬ አስባለው” እሱባለው ጌታቸው
ስለጨዋታው
“ጥሩ ነበር፡፡ 3-1 እየመራን ስለነበር የነሱን እንቅስቃሴ ገትተን ለማሸነፍ ነበር እቅዳችን፡፡ ተከላክለን ውጤት ለማስጠበቅ ነበር ወደ ጨዋታ የገባነው፡፡ የተሻለ ውጤት አምጥተናል ብዬ አስባለው፡፡ አሰልጣኞቻችን ያዘዙንን ስራ ነው የሰራነው፡፡ አሰልጣኞቻችን ያሳዩን ነገር ተግብረን ለመውጣት ነበር የሞከረነው፡፡”
ስለቀጣይ ተጋጣሚ
“በጥሩ ሁኔታ ለቀጣዩ ግጥሚያ የምንዘጋጅ ይሆናል፡፡ ዓላማችን ለማሸነፍ ነው፡፡ ማዳካሰጋር ለሚደረገው የአፍሪካ ዋንጫ እንደምናልፍ እርግጠኛ ነኝ፡፡ በጥሩ የድን መንፈስ እንደምናሸንፍ እርግጠኛ ነኝ፡፡”
የኢትዮጵያ ቡና አስተዋፅኦ
“በእኔ የእግርኳስ ህይወት የቡና አስተዋፅኦ ላቅ ያለነው፡፡ ኢትዮጵያ ቡና ማለት በእግርኳስ የሚያምን ክለብ ነው፡፡ ጥሩ ጥሩ አማካዮችን የያዘ ነው ለምሳሌ እንደኤልያስ ማሞ፣ ጋቶች ፓኖም፡፡ እኔም እነሱን እንደምተካ እርግጠኛ ነኘ፡፡ በዚሁም ለኢትዮጵያ ቡና ከ17 ዓመት በታች ቡድን አሰልጣኝ ታዲዮስ ተክሉ ምስጋና ማቅረብ እፈልጋለው፡፡”