በዩጋንዳ አስተናጋጅነት ለመጀመርያ ጊዜ በሚካሄደው የምስራቅ እና መካከለኛው አፍሪካ ሴቶች ዋንጫ ተሳታፊ የሚሆነው የኢትዮዽያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ከነሐሴ 15 ጀምሮ በድሬደዋ ዝግጅቱን እያደረገ ይገኛል፡፡
ሉሲዎቹ በቀን ሁለት ጊዜ ልምምድ በማካሄድ እና በአካባቢው ከሚገኙ ቡድኖች ጋር የአቋም መፈተሻ ጨዋታዎችን በማድረግ የሰነበቱ ሲሆን ከነገ ጀምሮ የልምምድ መርሃ ግብራቸውን ወደ አንድ ዝቅ እንደሚያደርጉ ለማወቅ ተችሏል፡፡
አሰልጣኝ መሰረት ማኒ ስብስባቸውን ከ32 ወደ 24 የቀነሱ ሲሆን ጥሪ ከተደረገላቸው ተጨዋቾች መካከል ዘቢብ ኃይለስላሴ እና ገነት አክሊሉ ባጋጠማቸው ከፍተኛ ጉዳት ከብሄራዊ ቡድኑ ውጪ ሆነዋል፡፡ ከሁለቱ በተጨማሪ ምስር ኢብራሒም ፣ ገነት ኃይሉ ፣ ብዙዬ ታደሰ እና ትግስት ዘውዴ የተቀነሱ ተጫዋቾች ናቸው፡፡ ከዚህ ቀደም ደግሞ ሐብታም እሸቱ እና ቅድስት ቦጋለ በግል ጉዳይ ከብሄራዊ ቡድኑ ውጪ መሆናቸው የሚታወስ ነው፡፡ ወደ ሴካፋ የሚያመሩት 23 ተጫዋቾች ሲሆኑ ከውድድሩ በፊት ጉዳት የሚያጋጥም ከሆነ በሚል 24ኛ ተጫዋች ተካቷል፡፡
ብሄራዊ ቡድኑ መስከረም 1 ቀን 2008 ከሚጀምረው ውድድር ቀደም ብሎ አንድ የወዳጅነት ጨዋታ እያፈላለገ ሲሆን ከካሜሮን ጋር የወዳጅነት ጨዋታ ለማድረግ ጥረት እየተደረገ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡
የ24 ተጫዋቾች ስብስብ
ግብ ጠባቂዎች
ሊያ ሽብሩ (ደደቢት) ፣ ማርታ በቀለ (መከላከያ) ፣ ታሪኳ በርገና (ድሬዳዋ ከተማ)
ተከላካዮች
አትክልት አሸናፊ (ቅዱስ ጊዮርጊስ) ፣ መስከረም ካንኮ (ደደቢት) ፣ ምህረት መለሰ (መከላከያ) ፣ ጥሩአንቺ መንገሻ (ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ) ፣ ፅዮን እስጢፋኖስ (ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ) ፣ እፀገነት ብዙነህ (ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ) ፣ አሳቤ ሙሶ (ዳሽን ቢራ) ፣ አረጋሽ ፀጋ (ሲዳማ ቡና)
አማካዮች
እመቤት አዲሱ (መከላከያ) ፣ ኤደን ሽፈራው (ደደቢት) ፣ ሰናይት ቦጋለ (ደደቢት) ፣ ብርቱካን ገብረክርስቶስ (ደደቢት) ፣ ፍቅርተ ብርሃኑ (መከላከያ) ፣ ብሩክታዊት ግርማ (ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ) ፣ ህይወት ደንጊሶ (ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ) ፣ ሰርካለም ቦጋለ (ዳሽን ቢራ) ፣ አዲስ ንጉሴ (ሀዋሳ ከተማ)
አጥቂዎች
ሎዛ አበራ (ደደቢት) ፣ ረሂማ ዘርጋ (ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ) ፣ ሽታዬ ሲሳይ (ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ) ፣ መዲና አወል (ቅድስት ማርያም ዩ.)