ለ2 አመት ከ6 ወር በዋልያዎቹ አሰልጣኝነት የቆዩት አሰልጣኙ ባለፈው ረቡእ የስንብታቸው ዜና ከተሰማ በኃላ ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን እና ለሱፐር ስፖርት አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
ከሱፐር ስፖርቱ ኮሊንስ ኦኪንዮ ጋር ባደረጉት ቆይታ በስንብታቸው እንዳልተከፉ ሲገልፁ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ባደረጉት ሰፊ ቆይታ ስንብቱን እንዳልጠበቁት ገልፀዋል፡፡
‹‹ የአሰልጣኝነት ስራ እጅግ አስቸጋሪ ነው፡፡ ሁልጊዜም የምትወደደው ከፍታ ላይ ስትሆን ብቻ ነው፡፡ ነገሮችን እንዳመጣጣቸው መቀበል አለብህ ፤ እኔም በስንብት ዜናው አልተደናገጥኩም፡፡ ›› ሲሉ ለሱፐር ስፖርት ተናግረዋል፡፡አሰልጣኙ ይህን ቢሉም በኢቲቪ ባደረጉት ቃለምልልስ ላይ ደግሞ ስንብቱን እንዳልጠበቁትና ካለወቅቱ እንደመጣባቸው ተናግረዋል፡፡
ሰውነት ቢሻው ለተወሰነ ጊዜ ከአሰልጣኝነት ተገልለው ለቤተሰባቸው ሰፊ ጊዜ እንደሚሰጡ ገልፀው ባለፉት ሁለት አመታት ከጎናቸው የቆመውን ህዝብ አመስግነዋል፡፡