ወላይታ ድቻን ከ ኢትዮጵያ ቡና ያገናኘው 6ኛው ሳምንት የኢትዮዽያ ፕሪሚየር ሊግ 1-1 በሆነ አቻ ውጤት ተፈጽሟል፡፡
ከፍተኛ የሆነ የተመልካች ቁጥር እና ድባብ በተስተዋለበት በዚህ ጨዋታ እምብዛም ሳቢ እንቅስቃሴ መመልከት አልተቻለም፡፡ በረጃጅም ኳስ ወደ ጎል ለመድረስ በሚደረግ ጥረት ብዙ ኳሶች መድረሻ ሳይኖራቸው ባክነው የቀሩበት እንቅስቃሴም የመጀመርያው አጋማሽ አሳይቶናል፡፡
ጨዋታው በተጀመረ ገና በ3ኛው ደቂቃ ኢትዮጵያ ቡናዎች ከመስመር የተሻገረውን ኳስ ወደ ግቅነት ቢቀይሩም ሳይጸድቅ በመቅረቱ ክስ አስይዘው ጨዋታው ቀጥሏል፡፡
ባለሜዳዎቹ ወላይታ ድቻዎች በፈጣን እንቅስቃሴ ኳሱን ተቆጣጥረው ተጭነው ለመጫወት ቢንቀሳቀሱም ይህ ነው የሚባል የጎል ሙከራ ማድረግ አልቻሉም ።
በአንፃሩም ኢትዮዽያ ቡናዎች ከሚታወቁበት በቅብብል ላይ የተመሰረተ እንቅስቃሴ በተለየ መልኩ በአብዛኛው ረጃጅም ኳሶችን ተጠቅመው ወደ ጎል ለመቅረብ ቢያስቡም 38ኛው ደቂቃ ኤልያስ ማሞ ከ16:50 ውጭ በቮሊ መቶት በግቡ አናት ለጥቂት ከወጣው ግሩም ሙከራ ውጭ ሌላ የጎል ሙከራ ሳያደርጉ የመጀመርያው አጋማሽ ያለግብ ተጠናቋል ።
በሁለተኛው አጋማሽ በሁለቱም በኩል ከመጀመርያው አጋማሽ በተሻለ ጥሩ የኳስ ፍሰት ፣ መልካም እንቅስቃሴ ቢያሳዩም እንደመጀመርያው አጋማሽ ሁሉ እንቅስቃሴያቸውን በግብ ሙከራ ማጀብ አልቻሉም፡፡
ከቆሙ ኳሶች የድቻን የጎል ክልል ሲፈትሽ የዋለው ኤሊያስ ማሞ በ61ኛው ደቂቃ ከርቀት መቶ የግቡ የውስጠኛው ብረት ገጭቶ የወጣው ኳስ የሚያስቆጭ አጋጣሚ ነበር ።
በ67ኛው ደቂቃ ላይ አላዛር ፋሲካና በዛብህ መለዮ በጥሩ ቅብብል ሰብረው በመግባት በዛብህ መለዮ ወደ ጎልነት በመቀየር ወላይታ ድቻን ቀዳሚ ማድረግ ችሏል።
ከጎሉ መቆጠር በኋላ ወደ ኋላ ያፈገፈጉት ድቻዎች ሙሉ ለሙሉ በኢትዮዽያ ቡና ብልጫ የተወሰደባቸው ሲሆን በ81ኛው ደቂቃ ላይ ኤልያስ ማሞ ከቀኝ መስመር ወደ ጎል ያሻማውን ኳስ አብዱልከሪም መሀመድ በግንባሩ ገጭቶ ወደ ጎልነት በመቀየር ቡናን አቻ አድርጓል።
ከግቡ መቆጠር በኋላ በቀሩት ጥቂት ደቂቃዎች ሁለቱም ቡድኖች የማሸነፍያ ግብ ለማስቆጠር ቁጭ ብድግ የሚያደርግ ፉክክር ቢያደርጉም ተጨማሪ ጎል ሳይቆጠር በአቻ ውጤት ተጠናቋል ።
በጨዋታው 380 ኪሎ ሜትር አቋርጠው የመጡት በርካታ ቁጥር ያላቸው የኢትዮዽያ ቡና ደጋፊዎች 90 ደቂቃውን ሙሉ ቡድናቸውን በህብረ ዝማሬ ሲያበረታቱ ውለዋል፡፡
የአሰልጣኞች አስተያየት
መሳይ ተፈሪ – ወላይታ ድቻ
” ኳሱን ተቆጣጥረን በእነሱ ላይ ብልጫ በመውሰድ አሸንፎ ለመውጣት ነበር አስበን የገባነው፡፡ ሆኖም ኢትዮዽያ ቡና በተለየ አጨዋወት መምጣቱ የፈለግነውን እንዳናደርግ አድርጎናል ፣ በተከታታይ ሁለት ጨዋታ በሜዳችን ነጥብ መጣላችን ጥሩ ባይሆንም በቀጣይ ድክመቶቻችን ላይ ጠንክረን በመስራት ወደ አሸናፊነት ለመመለስ ጥረት እናደርጋለን ። በተረፈ ከነበረው ጠንካራ ጨዋታ አንፃር አቻ መውጣታችን አያስከፋም”
ኒቦሳ ቩሴቪች – ኢትዮጵያ ቡና
“ጥሩ ጨዋታ ነበር:፡፡ የስታድየሙ ድባብ አስደሳች ነበር፡፡ የወላይታ ድቻ ተከላካዮች የመከላከል ብቃት አስገራሚ ነበር ። የሜዳው ለጨዋታ አመቺ አለመሆንም የፈለግነውን እንዳናደርግ አድርጎናል፡፡”
” የዕለቱ ሦስት ዳኞች በኢትዮዽያ ውስጥ ምርጥ የሚባሉ ዳኞች ናቸው፡፡ ለምን ያገባነውን ጎል እንደሻሩት አላውቅም ፤ እነሱ ቢጠየቁ መልካም ነው፡፡ በተረፈ ውጤቱ ጥሩ ነው፡፡”