በካፍ ቻምፒየንስ ሊግ 1ኛ ዙር የመልስ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከዶሊሲ ይዞት የተመለሰውን ወደ ምድብ ድልድል የመግባት ሰፊ እድል ወደ እውነትነት ለመቀየር ነገ በአዲስ አበባ ስታድየም 10:00 ላይ ኤሲ ሊዮፓርድስን ይገጥማል፡፡
ማክሰኞ አመሻሽ ላይ አዲስ አበባ የገቡት ፈረሰኞቹ ከረቡዕ ጀምረው ልምምዳቸውን ቀጥለው ለነገ የመልሱ ጨዋታ ዛሬ ከ8:05 ጀምሮ በአዲስ አበባ ስታድየም የመጨረሻ ልምምድ ያደረገ ሲሆን ለጨዋታው የሚጠቀምባቸው 18 ተጫዋቾችንም ለይቷል፡፡
ቀልል ያለ እና ቋሚ አስራ አንዱን በሚለይ ሁኔታ ለአንድ ሰአት ያህል የቆየ ከኳስ ጋር ያመዘነ እንቅስቃሴ እና የቆሙ ኳሶችን የመጠቀም ስራ የልምምዳቸው አካል ነበር ።
ከጉዳት ጋር በተያያዘ በጀመርያ ጨዋታ በጉልበቱ ላይ መጠነኛ ጉዳት ያጋጠመው ሮበርት ኦዶንካራ ከቡድኑ ጋር ለሁለት ቀናት ያህል ልምምድ ያልሰራ ቢሆንም ከትላንት ጀምሮ ከቡድኑ ጋር ሙሉ ልምምድ መጀመሩ ለቡድኑ እፎይታ የፈጠረ ሆኗል፡፡ ተስፈዬ አለባቸው በዛሬው እለት ልምምድ ላይ ተነጥሎ ብቻውን ሲሰራም ተመልክተናል። ከጉዳት ጋር የተያያዘ ሌላ ዜና የሌለ ሲሆን ምንተስኖት አዳነ በመጀመርያው ጨዋታ ላይ የቀይ ካርድ በመመልከቱ የነገው ጨዋታ የሚያልፈው ይሆናል ።
ሶከር ኢትዮዽያ ከቡድኑ ቁልፍ ተጨዋቾች ጋር ባደረገችው ቆይታ ጨዋታው ገና እንዳላለቀና ከሜዳ ውጭ ማሸነፋቸው እንደማያዘናጋቸው ገልፀው ደጋፊዉ ከጎናቸው እንዲሆን ጠይቀዋል፡፡ ታሪክ ለመርስራት ቆርጠው መነሳታቸውንም አያይዘው ጠቅሰዋል።
አሰልጣኝ ማርት ኑይ በነገው ጨዋታ ላይ የሚጠቀሙባቸውን 18 ተጫዋቾች የለዩ ሲሆን በመጀመርያው ጨዋታ በቀይ ካርድ ከሜዳ ከወጣው ምንተስኖት አዳነ በቀር ወደ ኮንጎ ያመሩት 17 ተጫዋቾች ለዚህም ጨዋታ ተካተዋል፡፡ አይቮሪያዊው አጥቂ ብሩኖ ኮኔ ምንተስኖትን ተክቶ በዝርዝሩ የተካተተ ተጫዋች ነው፡፡
ግብ ጠባቂዎች
ሮበርት ኦዶንካራ ፣ ዘሪሁን ታደለ
ተከላካዮች
ፍሬዘር ካሳ ፣ ደጉ ደበበ ፣ ሳላዲን ባርጌቾ ፣ አስቻለው ታመነ ፣ አበባው ቡታቆ ፣ መሃሪ መና
አማካዮች
ተስፋዬ አለባቸው ፣ ያስር ሙገርዋ ፣ ናትናኤል ዘለቀ ፣ አብዱልከሪም ኒኪማ ፣ በሃይሉ አሰፋ፣ ፕሪንስ ሲቬርኒሆ
አጥቂዎች
አዳነ ግርማ፣ ሳላዲን ሰዒድ፣ አቡበከር ሳኒ ፣ ብሩኖ ኮኔ
* ቅዱስ ጊዮርጊስ በመጀመርያው ጨዋታ በምንተስኖት አዳነ ግብ 1-0 አሸንፎ መመለሱ የሚታወስ ነው፡፡
* ጨዋታውን የሚመሩት አራቱም ዳኞች ከሱማልያ ሲሆኑ ኮሚሽነሩ ከሱዳን ናቸው፡፡
* ጨዋታው ነገ 10:00 በአዲስ አበባ ስታድየም ይደረጋል፡፡ የመግቢያ ዋጋውም የሚከተለውን ይመስላል፡፡
ክቡር ትሪቡን -1000 ብር
ጥላ ፎቅ – 200 ብር
ከማን አንሼ – 100 ብር
ከማን አንሼ (ያለ ወንበር) – 30 ብር
ካታንጋ – 20 ብር
ዳፍ / ሚስማር ተራ – 10 ብር