የሴቶች ፕሪምየር ሊግን የውድድር ዘመን ጉዞ የሚወስኑ የመሪዎቹ ፍጥጫዎች. . .

ከወትሮው በተለየ ፉክክር ፣ የተመልካች ትኩረት እና የቡድኖች ጥራት እያስመለከተን የሚገኘው የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 14ኛ ሳምንት ላይ ደርሷል፡፡ በዚህ ሳምንትም የሊጉን ጉዞ የሚወስኑ ሁለት ጨዋታዎችን ያስተናግዳል፡፡ በምድብ ሀ ደደቢት ከ አዳማ ከተማ ነገ ሲገናኙ አርብ ደግሞ በምድብ ለ በተመሳሳይ በሰንጠረዡ አናት ተከታትለው የተቀመጡት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ሀዋሳ ከተማ ይፋለማሉ፡፡

ደደቢት ከ አዳማ ከተማ

ቀን – ረቡዕ መጋቢት 13 ቀን 2009

ቦታ – አዲስአበባ ስታድየም

ሰአት – 11:30

የአምናው የሴቶች ፕሪምየር ሊግ ባለ ድል ደደቢቶች በዘንድሮው የውድድር ዘመን ከሚገኙበት ምድብ ሀ እስካሁን ካደረጓቸው 12 ጨዋታዎች ሁሉንም አሸንፈው 36 ነጥብ በማስመዝገብ ከምድቡ አናት ላይ ሲቀመጡ በ100% ግስጋሴያቸው በመቀጠል የአምናው የ13 ጨዋታ ያለመሸነፍ ሪከርድን ለማሻሻል የሁለት ጨዋታዎች እድሜ ቀርቷቸዋል ፤ ይህንንም ለማድረግ የነገውን ተጋጣሚያቸው የሆነውን ጠንካራውን አዳማ ከተማን ማሸነፍ ይጠበቅባቸዋል፡፡

በአንጻሩ ከጥሩነሽ ዲባባ አካዳሚ በተገኙ በርከት ባሉ ወጣት ተጫዋቾች እንደ አዲስ የተቋቋመው አዳማ ከተማ በዘንድሮው የውድድር ዘመን ክስተት መሆን ችሏል፡፡ አዳማዎች ካደረጓቸው 12 ጨዋታዎች በ2ቱ ብቻ ተሸንፈው በቀሪዎቹ 10 ጨዋታዎች አሸንፈው በ30 ነጥብ ከደደቢት በ6 ነጥብ ርቀው በምድብ ሀ ሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል፡፡

በሁለቱ ቡድኖች የመጀመሪያ ዙር እርስበርስ ግንኙነት ጠንካራ ፉክክር በታየበት ጨዋታ አዳማ ላይ ደደቢት በሎዛ አበራ ብቸኛ የፍፁም ቅጣት ምት ግብ 1-0 አሸንፎ መመለሱ የሚታወስ ነው፡፡

ሁለቱ ቡድኖች በሚያደርጉት ተጠባቂ ጨዋታ ላይ በሊጉ 22 ግቦችን አስቆጥራ በከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን የምትመራው ሎዛ አበራ እና ታታሪዋ ሰናይት ባሩዳ የሚመራው አስፈሪው የደደቢት የማጥቃት እንቅስቃሴ በጨዋታው ላይ ልዩነት ይፈጥራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ከመሀል እየተነሱ ግብ ማስቆጠር የሚችሉ አማካዮች ባለቤት የሆኑት የደደቢቶች የአማካይ ክፍል በጨዋታው ደደቢትን ወደ ድል ለመምራት ቁልፍ ይሆናሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በአዳማዎች በኩል በ10ግቦች የሊጉ 3ኛ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ የሆነችው የጥሩነሽ ዲባባ ወጣቶች አካዳሚ ፍሬዋ ሴናፍ ዋቁማ ለጠንካራው የደደቢት የተከላካይ ስፍራ ፈተና ትሆናለች ተብሎ ይጠበቀል፡፡ በአካል ብቃት እና የቴክኒክ ክህሎት የበለጸጉ እንደ ናርደዶስ ጌትነት ፣ ኢማን ሽመልስ እና አስካለ ገብረጻድቅን የያዘው አዳማ ለደደቢት በቀላሉ እጅ ይሰጣል ተብሎ አይጠበቅም፡፡

ከሁለት ሳምንት በፊት ድራማዊ ክስተቶች በተስተናገዱበትና ከሁለት ለባዶ መመራት ተነስተው ኢትዮጵያ ቡናን ካሸነፉበት ጨዋታ በኃላ ባሳለፍነው ሳምንት ሳይጠበቅ በሜዳቸው በጥረት 2-1የተሸነፉት አዳማ ከተማዎች ይህ ጨዋታ የምድቡ የበላይ ሆነው ለማጠናቀቅ በሚያደርጉት ፉክክር ላይ ወሳኝ ሚና ይኖረዋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በአጠቃላይ የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ በወቅቱ የሴቶች እግርኳስ ታላቅ ቡድን ደደቢት እና በወጣቶች የተሞላ የወደፊቱን ታላቅ ቡድን እየመሰረተ በሚገኘው አዳማ ከተማ መካከል የሚካሄድ ነው፡፡

[table id=237 /]

[league_table 18073]

ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከ ሀዋሳ ከተማ

ቀን – አርብ መጋቢት 15 ቀን 2009

ቦታ – አዲስአበባ ስታዲየም

ሰአት – 5:00

በምድብ ለ የሚገኙት ኢትዮጵያ ንግድ ባንክና ሀዋሳ ከተማ በ7 ነጥብ ልዩነት በ34 እና በ27ነጥብ 1ኛና 2ኛ በመሆን ተከታትለው በመምራት ላይ ይገኛሉ፡፡

ኢትዮጵያ ንግድ ባንኮች ካደረጓቸው 12 ጨዋታዎች በአንዱ ብቻ አቻ ተለያይተው ቀሪዎቹን አስራ አንድ ጨዋታዎች በድል በማጠናቀቅ 34 ነጥብ በመሰብሰብ እና ባለመሸነፍ ጉዟቸው ሲቀጥሉ ሀዋሳ ከተማዎች በዘጠኝ ጨዋታዎች አሸንፈው በቀሪ አራት ጨዋታዎች የሽንፈትን ፅዋ ተጎንጭተዋል፡፡

ኢትዮጲያ ንግድ ባንኮች በዘንድሮው የውድድር አመት ምንም እንኳን ስብስባቸው በጉዳት ቢሳሳም አሁንም ቢሆን ጨዋታዎችን ከማሸነፍ አላገዳቸውም፡፡ ነገርግን በተለይም ለተከታታይ አመታት የቡድኑ ሁነኛ ግብ አስቆጣሪ የሆነችው ሽታዬ ሲሳይ በጉዳት ከቡድኑ ከተለይች በኃላ ቡድኑን በተደጋጋሚ ጨዋታዎች ላይ ግቦችን ለማስቆጠር ሲቸገር ተስተውሏል፡፡

በአንጻሩ ሀዋሳ ከተማዎች ባሳለፍነው ሳምንት አዲስአበባ ከተማን 6-0 ሲረመርሙ ለብቻዋ 5 ግቦችን ማስቆጠር የቻለችውና በሊጉ በ18 ግቦች ሁለተኛ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ የሆነችውን አይናለም አሳምነውን የያዙት ሀዋሳዎች በተዋጣለት የማጥቃት አጨዋወት ንግድ ባንክን ይፈትኑታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በጥሩአንቺ መንገሻ በሚመራው የተረጋጋ የተከላካይ መስመር እና ከፍተኛ ልምድ ባለው የአማካይ ክፍል የሚተማመን ሲሆን በዘንድሮው የቡድኑ ጉዞ ላይ ምርጥ ግልጋሎት በማበርከት ላይ የምትገኘው ህይወት ደንጊሶም በጨዋታው ላይ ልዩነት ትፈጥራለች ተብሎ ይጠበቃል፡፡

ሀዋሳ ከተማ በአይናለም አሳምነው ላይ የተመሰረተ ፈጣን የማጥቃት እንቅስቃሴን ይተገብራል፡፡ ብዙዎች 18 ግቦች ያስቆጠረችው አይናለም ላይ ትኩረት ቢያደርጉም አብዛኛዎቹን ኳሶች ለግብ አመቻችታ ያቀበለችው ትርሲት መገርሳ ድንቅ አቋሟን እንደምታበረክት ትጠበቃለች፡፡

በሁለቱ ቡድኖች የመጀመሪያ ዙር ጨዋታ ሀዋሳ ላይ ኢትዮጲያ ንግድ ባንኮች በአማካይዋ ህይወት ዳንጌሶ ብቸኛ የቅጣት ምት ጎል ሀዋሳ ከተማን 1-0 አሸንፈው መመለሳቸው አይዘነጋም፡፡

[table id=241 /]

[league_table 18083]

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *