የኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪሚየር ሊግ 14ኛ ሳምንት ዛሬም ቀጥለው ተካሂደዋል፡፡ በጠዋት መርሃግብሮች ከሜዳቸው ውጪ የተጫወቱት ጌዲዮ ዲላ እና አርባምንጭ ከተማ ተጋጣሚዎቻቸውን ሲያሸንፉ የመሪዎቹ ትንቅንቅ በአቻ ውጤት ተጠናቋል፡፡
በቅድሚያ ረፋድ 3:00 በተደረገው ጨዋታ በታዳጊ ወጣቶች የተሞላው ጊዲዮ ዲላ ቅዱስ ጊዮርጊሶች በራሳቸው መረብ ላይ ባስቆጠሩት ብቸኛ ግብ 1-0 ማሸነፍ ችለዋል፡፡ ጠንካራና ተመልካችን ያዝናና ፉክክር በታየበት የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ መሰሉ አበራ በቅዱስ ጊዮርጊስ በኩል እንዲሁም ትንቢት ሳሙኤል በዲላዎች በኩል ጥሩ መንቀሳቀስ ችለዋል፡፡
በዚህም ውጤት መሠረት ጊዲዮ ዲላዎች ነጥባቸውን ወደ 23 አሳድገው ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ጋር በነጥብ በመስተካከል በጎል ክፍያ ተበልጠው በ4ኛ ደረጃ ላይ ተቀመጠዋል፡፡
በ5:00 የተገናኙት ልደታ ክፍለ ከተማ እና አርባምንጭ ከተማ ነበሩ፡፡ እምብዛም ሳቢ ያልነበረው የሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ዐእንግዶቹ አርባምንጭ ከተማዎች 4-1 አሸናፊነት ሊጠናቀቅ ችሏል፡፡ ለአሸናፊዎቹ አርባምንጮች ትዝታ ፈጠነ ሁለት ግቦችን ስታስቆጥር ቤተልሄም ጥላሁንና ህይወት ቀሪዎቹን ግቦችን ማስቆጠር ችለዋል፡፡
ጨዋታውን በአሸናፊነት ያጠናቀቀው አርባምንጭ ከተማ አሁንም በ15 ነጥብ 7ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡
ከሰአት 9፡00 የጀመረው የንፋስ ስልክ ላፍቶ ክ/ከተማ እና የቦሌ ክፍለ ከተማ ጨዋታ 2-2 በሆነ የአቻ ውጤት ተጠናቋል፡፡ ምስጋና ግርማ እና ምንትዋብ ዮሀንስ ለቦሌ ሲያስቆጥሩ ዘነበች ዘመዲ በግሩም ቅጣት ምት እንዲሁም ፍሬንሲ ዮሱፍ የንፋስልክን ግቦች አስቆጥረዋል፡፡
በተመሳሳይ 9፡00 ባህርዳር ላይ መከላከያን ያስተናገደው ጥረት 4-0 በሆነ ውጤት ተረምርሟል፡፡ ሄለን ሰይፉ ፣ ሄለን እሸቱ ፣ ብሩክታዊት አየለና ኩሪ ኦጥቁ የመከላከያን የድል ግቦች ከመረብ አዋህደዋል፡፡ በዚህም ውጤት መሠረት መከላከያ በኤሌክትሪክ ተነጥቆ የነበረውን የ3ኝነት ደረጃ ነጥቡን ወደ 25 አሳድጎ ዳግም ተረክቧል፡፡
አመሻሽ 11:30 ላይ በጀመረው የሳምንቱ ተጠባቂና የምድብ ሀ የአመቱ ወሳኝ ጨዋታ በተባለለት ጨዋታ የምድቡ መሪ ደደቢት አዳማ ከተማን አስተናግዶ ያለ ግብ በአቻ ውጤት ተለያይቷል፡፡
በጨዋታው የመጀመሪያ 15 ደቂቃዎች ደደቢቶች የተሻለ መንቀሳቀስ ቢችሉም ሰናይት ባሩዳ ያገኘቻቸውን ሁለት ግብ የማግባት አጋጣሚዎች የአዳማዋ ግብጠባቂ ልታድንባት ችላለች፡፡ የአዳማዋ ግብጠባቂ ኮከብ ሆና ባመሸችበት የመጀመሪያው አጋማሽ ደደቢቶች ተጨማሪ የግብ ማግባት አጋጣሚዎችን መፍጠር ቢችሉም ግብጠባቂዋ የምትቀመስ አልሆነችም፡፡
በመጀመሪያው አጋማሽ በጥልቀት በመከላከልና በመልሶ ማጥቃት የሚገኙ አጋጣሚዎችን ለመጠቀም አስበው ወደ ሜዳ የገቡ የሚመስሉት አዳማ ከተማዎች ፊት ላይ የምትገኘው አጥቂዋ ሲናፍ ዋቆማ በበርካታ አጋጣሚዎች ከተከላካይና ከግብ ጠባቂ በቀጥታ የሚላኩ ኳሶችን ተቆጣጥራ ወደፊት ለመሄድ በምታደርገው ጥረት ከሌሎች የቡድን አጋሮቿ በቂ ድጋፍ ባለማግኘቷ ኳሶቹ ሲበላሹ ተስተውሏል፡፡
በሁለተኛው አጋማሽ ጅማሮ ላይ ጫና መፍጠራቸውን የቀጠሉት ደደቢቶች በሁለት አጋጣሚዎች በአዳማ ተከላካዮች ስህተት በመታገዝ ያገኙትን እድል በሎዛ አበራና ሰናይት ቦጋለ ወደ ግብ ቢሞከሩም የግቡ አግዳሚና ቋሚ ግብ ከመሆን ታድጓቸዋል፡፡
በአዳማዎች በኩል ተቀይራ የገባችው አይዳ ኡስማን በግሏ የደደቢት ተከላካዮችን ፍጥነት እና ጉልበቷን ተጠቅማ በተደጋጋሚ ስታስጨንቃቸው ተስተውሏል፡፡ በዚህም በስታዲየሙ ከተገኘው ተመልካች ከፍተኛ አድናቆት ተችሯታል፡፡ ከጨዋታው መጠናቀቅ በኃላም በስታዲየሙ የተገኘው ተመልካች ለአዳማ ከተማ ቡድን አባላት እጅግ ሞቅ ያለ የሞራል ድጋፍ አድርጎላቸዋል፡፡
ውጤቱን ተከትሎ በዘንድሮው የውድድር ዘመን ያደረጋቸውን 12 ጨዋታዎች በሙሉ ያሸነፈው ደደቢት ተከታታይ የድል ጉዞው በአዳማ ዛሬ ሲገታ በተመሳሳይ በሁሉም ጨዋታዎች ግብ ስታስቆጥር የቆየችው ሎዛ አበራም ዛሬ ግብ ሳታስቆጥር ወጥታለች፡፡
በውጤቱ መሠረት ደደቢት አሁንም በ37 ነጥብ በመሪነቱ ሲቀጥል ተከታዩ አዳማም በ31 ነጥብ በ2ኛ ደረጃ ላይ ይገኛል፡፡
[table id=237 /]
[league_table 18073]
[table id=241 /]
[league_table 18083]