ቻምፒየንስ ሊግ | ኤስፔራንስ ዛሬ አዲስ አበባ ስታድየም ላይ ልምምዱን አድርጓል

ባሳለፍነው ሐሙስ ባላንጣውን ኤቷል ደ ሳህልን 3-0 በመርታት የቱኒዚያ ሊግ 1ን ለ27ኛ ጊዜ ዋንጫ ያነሳው ኤስፔራንስ ደ ቱኒዝ ቅዱስ ጊዮርጊስን ከመግጠሙ በፊት የመጨረሻ ልምምዱን አዲስ አበባ ስታዲየም ላይ ሰርቷል፡፡

የቱኒዙ ክለብ ልምምዱን የሰራው ከ10፡20 ጀምሮ ሲሆን በልምምዱ ላይ 21 ተጫዋቾች ተሳትፈዋል፡፡ ኳስ ወደ መስመር ማውጣት እና እንዲሁም አማካዮቹ ፎሴኒ ኩሊባሊ እና ፈርጃኒ ሳሲ ላይ ያተኮሩ ልምምዶች ሰርተዋል፡፡

በ67 አመቱ አንጋፋ ቱኒዚያዊው አሰልጣኝ ፋውዚ ቤንዛርቲ የሚሰለጥነው ቡድኑ በማክሰኞው የቻምፒየንስ ሊግ በመስመር ማጥቃትን መሰረት አድርጎ ለመጫወት ያለመ እንቅስቃሴ በልምምድ ወቅት ሲያደርግ ታይቷል፡፡

ቀለል ያለ የነበረው የኤስፔራንስ ልምምድ ላይ ወሳኝ ተጫዋቾች የሆኑት ፋክረዲን ቤን የሱፍ፣ ሞይዝ ቤን ሻሪፋ፣ ጠሃ ያሲን ኬኔሲ፣ አኒስ ባድሪ፣ ኢሃብ ምባረኪ እንዲሁም ሰዓድ ባጉሪ ተሳትፈዋል፡፡

የቅዱስ ጊዮርጊስ እና ኤስፔራንስ የምድብ ሁለተኛ ጨዋታ ማክሰኞ 10፡00 ሰዓት ላይ በአዲስ አበባ ስታድየም ይደረጋል፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *