የ2009 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የመጨረሻ ሳምንት ጨዋታዎች በአዲስ አበባ እና በክልል ከተሞች በእኩል ሰዐት ተደርገው በ8 ጨዋታዎች 16 ግቦች ተቆጥረው እና ሁለት ተጨማሪ ወራጅ ክለቦች ተለይተው የውድድር አመቱ ተጠናቋል ።
አአ ስታድየም ላይ አትዮጵያ ነግድ ባንክን የገጠመው ቅዱስ ጊዮርጊስ 1-0 በማሸነፍ የመዝጊያ ስነስርአቱን በድል አድምቀዋል፡፡ ባለፉት ተከታታይ ጨዋታዎች ድንቅ አቋሙን ያሳየው ብሩኖ ኮኔ ብቸኛዋን የድል ግብ ሲያስቆጥር ውጤተቱኖ ተከትሎ ንግድ ባንክ ከሊጉ መውረዱን አረጋግጧል፡፡
ሶዶ ላይ በተካሄደው ሌላው ጨዋታ ወላይታ ድቻ ደደቢትን 4-2 በሆነ ውጤት በመርታት በቀጣይ አመት በፕሪምየር ሊጉ መቆየቱን ያረጋገጠበትን ውጤት ሲያስመዘግብ የደደቢቱ ጌታነህ ከበደም የዮርዳኖስ አባይን ሪከርድ በመስበር በ25 ጎሎች በአንድ የውድድር አመት በርካታ የሊግ ጎል ያስቆጠረ ተጫዋች ለመሆን በቅቷል፡፡
በጨዋታው ሙሉ ብልጫ ወስደው ለነበሩት ወላይታ ድቻዎች በእንዳለ መለዮ ላይ በተሰራ ጥፋት በተገኘውን የፍፁም ቅጣት ምት አላዛር ፋሲካ የመጀመሪያውን ግብ በ16ኛው ደቂቃ ሲያስቆጥር ከ5 ደቂቃዎች በኋላም ተመስገን ዱባ ፈቱዲን ጀማል ከማዕዘን ያሻማውን ኳስ በግንባሩ በማስቆጠር የቡድኑን መሪነት ወደ ሁለት ከፍ አድርጎታል። ድቻዎች ከእረፍት በፊት በአላዛር ፋሲካ አማካይነት ሶስተኛ ጎል በማከልም የቀረውን ደቂቃ ያለጭንቀት ለመጨረስ የሚያስችላቸውን ውጤት በጊዜ ማስመዝገብ ችለው ነበር። ሆኖም በከፍተኛ ደረጃ ሲጠበቅ የነበረው እና በስፍራው ከተገኘው ደጋፊ ማበረታቻ ሲደረግለት የነበረው ጌታነህ ከበደ በ45 እና 54ኛው ደቂቃ ላይ ያስቆጠራቸው ግቦች የባለሜዳዎቹን መሪነት ወደ አንድ የቀነሰ ነበር። ነገር ግን በጨዋታው ምርጥ እንቅስቃሴ ያደረገው ተመስገን ዱባ ለራሱ ሁለተኛውን እና ለቡድኑ አራተኛውን ግብ በ74ተኛው ደቂቃ ላይ በማስቆጠር የቡድኑን የበላይነት ማረጋገጥ ችሏል። የአሰልጣኝ መሳይ ተፈሪ ቡድንም በዚህ ሁኔታ የውድድር አመቱን በ36 ነጥብ 9ኛ ደረጃን በመያዝ ጨርሷል ።
ሌላው የመውረድ ስጋት አንዣቦበት የነበረው ኢትዮ ኤሌክትሪክም ሀዋሳ ላይ በጋዲሳ መብራቴ በተቆጠረበት ግብ ቢመራም በአምበሉ አዲስ ነጋሽ የፍፁም ቅጣት ምት ጎል አቻ በመሆን ሊጉን በ33 ነጥብ 13ኛ ደረጃ ላይ ሆኖ ሲያጠናቅቅ ተጠባቂ በነበረው ጨዋታ እስከ 80ኛው ደቂቃ ድረስ በሊጉ ሚያቆየውን የአቻ ውጤት ይዞ የቆየው ጅማ አባ ቡና በ 81ኛው ደቂቃ የሀብታሙ ወልዴ ጎል ምክንያት በመሸነፉ ከኤሌክትሪክ በ 1 ነጥብ አንሶ በ14ኛ ደረጃ ላይ በመቀመጥ ከሊጉ ተሰናብቷል። አባ ቡናን መርታት የቻለው ድሬደዋ ከተማ በበኩሉ ባሳካው ሶስት ነጥብ በመታገዝ በ35 ነጥቦች 11ኛ ደረጃን ይዞ ሲያጠናቅቅ ሰበታ ላይ ከኢትዮጵያ ቡና ያለግብ የተለያየው አርባምንጭ ከተማ በበኩሉ ከድሬደዋ በመቀጠል በ34 ነጥቦች 12ኛ ደረጃን ይዞ አጠናቋል ።
ይርጋለም ላይ መከላከያን ያስተናገደው ሲዳማ ቡና በበኩሉ በ32ኛው ደቂቃ ላይ በአዲስ ግደይ ቀዳሚ ሆኖ በማራኪ ወርቁ በ49ኛው ደቂቃ በተቆጠረበት ግብ ጨዋታውን በአቻ ውጤት ሲያጠናቅቅ በጨዋታው መስፍን ኪዳኔ እና ሰንደይ ሙትኩ በፈጠሩት ፀብ በቀይ ካርድ ከሜዳ ወጥተዋል። ሲዳማም መከላከያን ማሸነፍ ባለመቻሉ አንድ ደረጃ በመንሸራተት ሊጉን በ4ኝነት አጠናቋል። የሲዳማን ወደ አራተኝነት መውረድ ተከትሎም በታፈሰ ተስፋዬ እና ሱራፌል ዳኛቸው ጎሎች በመታገዝ ፋሲል ከተማን 2 ለ 1 መርታት የቻለው አዳማ ከተማ በሊጉ ሰንጠረዥ ላይ ለሶስተኛ ተከታታይ አመት የሶስተኛነትን ቦታ ማሳካት ችሏል። በሌላኛው የክልል ጨዋታም መውረዱን ያረጋገጠውን አዲስ አበባ ከተማን ያስተናገደው ወልድያ በያሬድ ብርሀኑ የ6ተኛ ደቂቃ ጎል በማሸነፍ ነጥቡን 37 በማድረስ እና 7ኛ ደረጃን በመያዝ ዘንድሮ ሊጉን ከተቀላቀሉ ክለቦች መሀል ፋሲል ከተማን በመከተል በሊጉ ወገብ ላይ መጨረስ ችሏል።
የደረጃ ሰንጠረዥ
ቻምፒዮን
ቅዱስ ጊዮርጊስ የ2009 ቻምፒዮንነቱን አስቀድሞ ያረጋገጠ ሲሆን ሊጉ በ1936 ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ ለ29ኛ ጊዜ በ1990 በአዲስ መልክ ከተዋቀረበት ጊዜ አንስቶ ደግሞ ለ14ኛ ጊዜ ዋንጫውን ማንሳት ችሏል፡፡
ወራጅ ቡድኖች
አአ ከተማ አስቀድሞ መውረዱን ያረጋገጠ ሲሆን ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከ18 የውድድር ዘመናት ቆይታ በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ከፕሪምየር ሊጉ ወርዷል፡፡ ዘንድሮ ሊጉን የተቀላቀለው ጅመማ አባ ቡናም 3ኛው ወራጅ ቡድን ነው፡፡
ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ
ጌታነህ ከበደ በ25 ግቦች የሊጉን ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነት ክብር አግኝቷል፡፡ በ2003 እና 2005 ከፍተኛ ጎል አስቆጣሪ ሆኖ ያጠናቀቀው ጌታነህ ለ3ኛ ጊዜ ክብሩን በማግኘት ከዮርዳኖስ አባይ ጋር መስተካከል ችሏል፡፡ በአንድ አመት በርካታ ጎል በማስቆጠርም የዮርዳኖስ አባይን የ24 ጎል ሪከርድ ሰብሯል፡፡
የኮከቦች ሽልማት
የኢትዮጵያ እገግርኳስ ፌዴሬሽን በስሩ የሚያካሂዳቸውን 6 ሊጎች ኮከቦች በጋራ ሐምሌ 25 እንደሚሸልም በማስታወቁ ከዚህ ቀደም በውድድሩ የመዝጊያ ቀነኒሳና ይሰጥ የነበረው ሽልማት ቀርቷል፡፡