ጅማ አባ ጅፋር አዲስ አሰልጣኝ ሾመ

ከአሰልጣኝ ጳውሎስ ጌታቸው ጋር በቅርቡ የተለያየው ጅማ አባ ጅፋር በዛሬው ዕለት አዲስ አሰልጣኝ ሾሟል።

በታሪኩ ለመጀመርያ ጊዜ በተሳተፈበት ዓመት የፕሪምየር ሊጉን ዋንጫ ካነሳ ባኋላ በተለያዩ ችግሮች የተነሳ አስቸጋሪ ወቅቶችን እያሳለፈ የሚገኘው ጅማ አባ ጅፋር በቅርቡ ከዋና አሰልጣኙ ጳውሎስ ጌታቸው ጋር በመለያየት በጊዜያዊ አሰልጣኝ ሲመራ መቆየቱ ይታወቃል።

አዲስ አሰልጣኝ ለመቅጠር ሲያፈላልግ የቆየው ክለቡ በዛሬው ዕለት በፌዴሬሽን በመገኘት አሰልጣኝ ፀጋዬ ኪዳነማርያምን በማስፈረም መሾሙን አረጋግጧል።

ጅማ አባ ጅፋር ቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ እስካሁን ባድጋቸው አስር ጨዋታዎች አንድም ጨዋታ ማሸነፍ ሳይችል በአራት ጨዋታ አቻ ወጥቶ በስድስት ጨዋታ ሽንፈት አስተናግዶ የመጨረሻ ግርጌ የሚገኝ ሲሆን በሊጉ ልምድ ያላቸው አሰልጣኝ በመቅጠር ከቀጠናው ለመውጣት ተስፋ አድርጓል።

አሰልጣኝ ፀጋዬ ኪዳነ ማርያም ከዚህ ቀደም ትራንስ ኢትዮጵያ፣ ሐረር ቢራ፣ ኢትዮጵያ ቡና፣ ንግድ ባንክ፣ አርባምንጭ እና ሀድያ ሆሳዕናን ማሰልጠናቸው ይታወቃል።


© ሶከር ኢትዮጵያ