ወልቂጤ ከተማ ሁለገቡን ተጫዋች አስፈርሟል

በተለያዩ ቦታዎች መጫወት የሚችለው ሔኖክ ኢሳይያስ ወልቂጤ ከተማን በአንድ ዓመት ውል ተቀላቅሏል።

በአዲሱ አሰልጣኝ ሙሉጌታ ምህረት መሪነት በርከት ያሉ አዳዲስ ተጫዋቾችን በመያዝ በክለቡ ከነበሩ ነባሮች ጋር በማቆራኘት የቅድመ ውድድር ዝግጅትን በሀዋሳ ከተማ እየከወኑ የሚገኙት ወልቂጤ ከተማዎች አስራ አራተኛ ፈራሚያቸው በማድረግ በሦስት የተለያዩ ቦታዎች ላይ መጫወት የሚችለውን ሔኖክ ኢሳይያስን በአንድ ዓመት ውል የግላቸው አድርገዋል።

በአማካይ እና ተከላካይ ስፍራ ላይ በመጫወት እግር ኳስን ቢጀምርም በሒደት በመስመር አጥቂነት በመጨረሻም በግራ መስመር ተከላካይነት በደደቢት ፣ ጅማ አባጅፋር ፣ መቐለ 70 እንደርታ ፣ ወላይታ ድቻ ፣ ድሬዳዋ ከተማ እና ያለፉትን ሁለት የውድድር ዘመናት ደግሞ በባህርዳር ከተማ እየተጫወተ የነበረው ሔኖክ በእግር ኳስ ህይወቱ ሰባተኛ ክለቡ ወልቂጤ ከተማ ሆኗል።