የአሰልጣኞች አስተያየት | ኢትዮጵያ መድን 0-0 ኢትዮ ኤሌክትሪክ

“ካለብን ችግር አንጻር አለመሸነፋችን በራሱ ትልቅ ነገር ነው።” አሰልጣኝ ገብረመድን ኃይሌ

“በዕረፍት ጊዜው የጎደሉንን ነገሮች አስተካክለን እንመጣለን ብዬ አስባለሁ።” አሰልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታ

የሶስተኛ ሳምንት ሁለተኛ ጨዋታ የሆነው የኢትዮጵያ መድን እና የኢትዮ ኤሌክትሪክ ጨዋታ ያለ ጎል ከተጠናቀቀ በኋላ የሁለቱም ክለብ አሰልጣኞች የሚከተለውን አስተያየት ለሶከር ኢትዮጵያ አጋርተዋል።

አሰልጣኝ ገብረመድኅን ኃይሌ – ኢትዮጵያ መድን

ለተከታታይ ጊዜ ግብ ማስቆጠር ስላልቻሉበት ጨዋታ…

”ዛሬ እንኳን ሙሉ በሙሉ በመከላከል ላይ ያተኮረ ጨዋታን ተጠቅሟል ተጋጣሚያችን ግን ያንን ፔኔትሬት ማድረግ ነበረብን። የምንችለውን ያህል ፔኔትሬት ለማድረግ ጥረት አድርገናል። አጋጣሚዎችን ሚስ ማድረጋችን ትልቁ ችግር ነበር ግን አሁን ካለብን ችግር አንጻር ይሄ አለመሸነፋችን በራሱ ትልቅ ነገር ነው ቀስ በቀስ የታመሙትም ሲመጡ የተሻለ ነገር  ይታያል ብዬ አስባለሁ።”

ስለ ጋቶች ፓኖም የመጀመሪያ ጨዋታ…

”ጥሩ ነው በአንዴ ነው የተዋሃደው ያው ኖርማሊ ብሔራዊ ቡድንም ስለምንተዋወቅ ተመሳሳይነት ያለውን ሥራ ስለምንሠራ በጣም ጥሩ እንዲያውም ዛሬ በጣም ብዙ ደቂቃ ተጫውቷል እና ከተጫወተው እና ካረፈው አንፃር ሲታይ በጣም ጥሩ ነው”

ከባለፉት ሁለት አመታት የቡድኑ አጀማመር አንፃር ዘንድሮ እንዴት ነው?

”ያው ዓምና አጀማመራችን ጥሩ አልነበረም። በሁለተኛ ጨዋታ ሽንፈት ነበር ቀጥሎም አቻ ፣ ሽንፈት አጋጥሞናል። በሂደት ነው ግራጁዋሊ እየጠነከረ እየጠነከረ እየዳበረ ነው የሚመጣው የእኛ ቲም። ሁሉንም ነገር የመረዳት ሁኔታቸው እና አንድ ላይ የመዋሃድ ነገራቸው ገና ልጆች ናቸው። ብዙ ልጆች አሉ ሀምሳ በሀምሳ ነው ሲኒየሩ እና ወጣቱ እና በዚህ ሁኔታ ይህ ሚጠበቅ ነው።”

አሰልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታ – ኢትዮ ኤሌክትሪክ

ተከታታይ ጨዋታቸውን ያለ ጎል ስለማጠናቀቃቸው…

”ይህ የቡድኔ ጥንካሬ ነው እንደ ቡድን ነው የማጠቃው እንደ ቡድን ነው የምከላከለው ስለዚህ የቡድኑ ጥንካሬ ስለሆነ በጣም ጥሩ ነገር  ነው ግን አሁንም አታኪንግ ሲቹዌሽኖች ላይ የሚቀሩን ነገሮች አሉ። ያገናቸውን ኳሶችን አልተጠቀምናቸውም። ጥሩ ጥሩ ኳሶችን አግኝተን ነበር ወደ ጎል የሚቀየሩ ግን አልተጠቀምናቸውም። ከሽንፈት መጥተን ፕሮግረስ አለው ቡድኑ አንዳንድ ነገር አስተካክለን የተሻለ ነገር እናደርጋለን ብዬ አስባለሁ በዚህ የዕረፍት ጊዜ ውስጥ።”

የመጀመሪያ ጨዋታ ሽንፈት ከዛ በኋላ ተከታታይ አቻ ፤ የቡድንህ ሂደት ምን ላይ ነው?

”ዲፌንሲቭ ኦርጋነዜሺናችን በጣም ጥሩ ነው በትራንዝሺንም የምንሄዳቸው ነገሮች በጣም ጥሩ ናቸው ለጌሞቹ ሙሉ ኮንሰንትሬሽን ሰጥተዋል እና ከተለያየ ቲም እነሱን በማዋሃድ የተሻለ ነገር የማድረግ አቅም አላቸው በጣም ጥሩ አቅም አላቸው። እነሱ ላይ ሰርተን ጥሩ ነገር እናደርጋለን ብዬ አስባለው። ህብረታቸው የመከላከልም የማጥቃትም ነገራቸው ትልቅ ስለሆነ ይሄንን ነገር ልጆች ናቸው ወጣቶች ናቸው ከዚህ በላይ ያደርጉልኛል ብዬ አስባለው አሁንም በዕረፍት ጊዜው የጎደሉንን ነገሮች አስተካክለን እንመጣለን ብዬ አስባለሁ።”

በዕረፍት ጊዜው ስለታሰቡ ዝውውሮች…

“አንዳንድ ቦታዎች ላይ ካገኘሁ እገባለሁ ብዬ አስባለሁ። ይሄንን ነገር ዐይቼ የተሻሉ ልጆች ላይ እገባለው አለዚያ ባሉኝ ልጆች ላይ ሠርቼ የተሻለ ነገር አደርጋለሁ።”