ግርማ ሀ/ዮሃንስ (ኢትዮጵያ)
“ያገኘነው ውጤት በልጆቻችን ከፍተኛ ጥረት በመሆኑ እኔም ራሱ ተደንቄበታለሁ። ምክኒያቱም በብዙ መልኩ የጋና ብሔራዊ ቡድን ጥሩ አቋም አለው። የእኛ ልጆች በተነገራቸው መሠረት በመስራታቸው የመጣ ውጤት በመሆኑ በጣም ደስ ብሎኛል።”
“ከእረፍት በኋላ ልንከላከል ፈልገን አይደለም፤ የተጋጣሚያችን ጫና ነው ያን የፈጠረብን እንጂ እኛ የፈለግነው በነሱ ሜዳ ላይ ኳስን ይዞ ለመጫወት ነበር።”
“ለመልሱ ጨዋታ ከአየር ፀባዩ ጀምሮ አጨዋወታችን ምን መሆን አለበት የሚለው ሌላ ዝግጅት የሚፈልግ ነው። በመልሱ ጨዋታ ኣሜ ላይ ብቻ ያተኮረ ቡድን እንዳይኖረን የራሳችንን ስራ ሰርተን እንገባለን።”
“ጨዋታው ቀናት ሲቀሩት አዳዲስ ተጫዋቾች ማካተታችን ችግር አልፈጠረብንም። የመጀመሪያው ጨዋታ ላይ የተጠቀምነውን ቡድን ይዘን ቀጥለን ቢሆን የተሻለ ቅንጅት ይኖረን ነበር ብዬ አስባለን። ይኼኛውም ቡድን ቢሆን ገና ብዙ የሚቀሩት ነገሮች አሉ።”
“ከደካማ ቡድን ጋር ከመጫወት ይልቅ ከጠንካራ ቡድን ጋር መጫወት ይሻላል። ስለዚህ ጋና ጠንካራ ቡድን መሆኑ እኛን ጠቅሞናል፤ ምክኒያቱም አቅምን አውጥቶ ለመጫወት የሚያስችል በመሆኑ። ጋናን ከመሰለ ጠንካራ ቡድን ጋር ለመጫወት የቻልንበት ህብረት ለኛ በጣም ጥሩ ነው። ወደፊት ደግሞ ይህንን ቡድን ይበልጥ እያዋሃድን ስለምንሄድ የተሻለ ነገር እንሰራለን ብለን እናምናለን።”
ዲዲ ድራማኒ (ጋና)
“በርካታ የምዕራብ አፍሪካ ቡድኖች ከባህር ወለል በላይ ትልቅ ከፍታ ወዳለው የምስራቁ የአህጉሪቷ ክፍል ሲሄዱ የሚገጥማቸው ችግር ይገጥመናል ብለን አስበን ነበር። ቀደም ብለን ወደ ኢትዮጵያ በመምጣት የአየር ሁኔታውን ለመልመድ ፍላጎት የነበረን ቢሆንም ይህንን ማድረግ አልቻልንም። ስለዚህ በጨዋታው መገባደጃ ላይ ችግር እንዳይገጥመን ጉልበታችንን ቆጥበን ለመጫወት ሞክረናል። ነገርግን ጨዋታው ከመጀመሩ በገቡብን ሁለት ግቦች ምክኒያት ገፍተን ለመጫወት ተገደናል፤ የመልሱን ጨዋታ ቀላል ለማድረግም ቢያንስ አንድ ግብ ለማስቆጠር ሙከራ እያደረግን ነበር።”
“የኢትዮጵያ እግርኳስ ሁሌም እንደምናውቀው በቴክኒክ ብቃት ላይ ያተኮረ ነው። ባለፈው ሐምሌ ወር ላይ የሴቶችን ከ20 ዓመት በታች ቡድን ይዤ እዚህ መጥቼ ነበር። የአፍሪካ እግርኳስ ፌዴሬሽን በክለቦች ምዝገባ ላይ በአዲስ አበባ በነበረው ስልጠና ላይም በኢንስትራክተርነት ተገኝቼ ነበር። ስለዚህ ለኢትዮጵያ እግርኳስ አዲስ አይደለሁም። ለኢትዮጵያ እግርኳስም ትልቅ ክብር አለኝ። በቂ ስራ ከተሰራበትም ከጥቂት ጊዜ በኋላ ኢትዮጵያ ከአፍሪካ ትልቅ የእግርኳስ ሃገራት አንዱ እንደምትሆን አስባለሁ።”
“ተጫዋቾቼ በሰሩት የግል ስህተት ምክኒያት ግቦች ተቆጥረውብናል። እንደዚህ አይነት ስህተቶች እንዳይፈጠሩ በልምምድ ወቅት ሰፊ ጊዜ ወስዶ መስራት ይጠይቃል። ተጫዋቾቹ ወጣት ናቸው፤ ስህተት ቢሰሩ እንኳን ከስህተታቸው ተምረው የተሻለ ተጫዋች ይሆናሉ ብዬ አስባለሁ።”
“በመልሱ ጨዋታ ግብ ሳይቆጠርብን በአንድ ግብ ብቻ ማሸነፍ ወደ ቀጣዩ ዙር ያሳልፈናል። በዚህ ጨዋታ በርካታ ዕድሎችን መፍጠር መቻላችን የመልሱን ጨዋታ ማሸነፍ እንደምንችል እምነት የሰጠን ሆኗል። የኢትዮጵያ ወጣት ቡድንም ቢሆን ጥሩ ተፎካካሪ ሆኖ ነው የሚመጣው። ነገርግን ድክመቶቻችንን በማረም ጠንካራ ሆነን በመቅረብ ጨዋታውን እናሸንፋለን።”