በሃይሉ አሰፋ ከብሄራዊ ቡድን ስለመቀነሱ ይናገራል ፤ አሰልጣኝ ገብረመድህን ሃይሌም ምላሽ ሰጥተዋል

የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከሌሶቶ ጋር ለሚያደርገው የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ጨዋታ ዝግጅት 25 ተጫዋቾችን በመጥራት ሰኞ ልምምድ ጀምሯል፡፡

በአሰልጣኝ ገብረመድህን ሃይሌ ስብስብ ከተካተቱት ተጫዋቾች አንዱ የነበረው በሃይሉ አሰፋ ተቀንሶ በምትኩ የደደቢቱ ሽመክት ጉግሳ ተመርጧል፡፡

በሃይሉ ለመቀነሱ በምክንያትነት የቀረበው ጉዳት ቢሆንም ለመቀነስ የሚያበቃ ጉዳት እንዳላጋጠመው ያለውን ቅሬታ ለሶከር ኢትዮጵያ ተናግሯል፡፡

” መቀነሴን የሰማሁት ከማህበራዊ ድረ-ገፅ ነው፡፡ በመጀመርያ ጉዳት እንዳለብኝ ልጠየቅ ይገባል፡፡ ነገር ግን ጉዳቴን ሳይጠይቁ በኔ ምትክ ሌላ ተጫዋች ጠርተዋል፡፡ እኔ ደግሞ አሰልጣኙ እንዲወቀስ ስለማልፈልግ ደውዬ አሞኛል ብዬ ሪፖርት አደረግኩ፡፡ ከጊዮርጊስ ጋር ወደ ሱዳን ተጉዣለሁ ፤ ልምምድም ሰርቻለሁ፡፡ ይህ ነው እኔ ጋር ያለው ነገር፡፡” ሲል አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡

picsart_1462210573019.jpg

አሰልጣኝ ገብረመድህን በበኩላቸው በሃይሉን አናግረውት እንዳላገገመ በመግለፁ እንደቀነሱት አብራርተዋል፡፡

” መጎዳቱንና የጡንቻ መሳሳብ ችግር እንዳለበት ከዚህ በፊትም አውቅ ነበር፡፡ አዲስ አበባም ጨዋታ ላይ ተቀይሮ ወጥቷል፡፡ ስለዚህ ጉዳት ቢሆን ነው ብዬ ገመትኩ፡፡  ስመርጠው ቢያንስ ያገግማል ብዬ ነው፡፡ ነገር ግን ሱዳን ላይም አልተጫወተም፡፡ ያገኘሁትም መረጃ ቢሆን ጉዳት ላይ እንደሆነ ነው። በሃይሉ እስኪመጣ መዘጋጀት ስለነበረብኝም ነው ሽመክትን የጠራሁት፡፡

“ከሱዳን መልስ አዲስ አበባ እንደገቡ ደውሎልኝ አሞኛል ብሎኛል፡፡ ታዲያ ካመመህ ለምን ሄድክ? መታመምህንስ ለምድነው ያልነገርከኝ? ስለው  “አይ አገግማለሁ ብዬ ነበር ፤ አልሆነልኝም” ቃል በቃል ይህን ነው ያለኝ፡፡ ካላገገመ ምን ማድረግ ይቻላል፡፡ ” ብለዋል፡፡

አሰልጣኝ ገብረመድህን አክለውም የጉዳት ችግር ከሌለበት በግልፅ ሊናገር እንደሚገባ ገልፀዋል፡፡

” እኛ ኦፊሻል ያደረግነው ነገር የለም፡፡ ከእኛ የሰማው ምንም ነገር ሳያገኝ መቀነሱን በምን አወቀ? በአንዳንድ ሚዲያና በማህበራዊ ድረገፅ ላይ ሊወራ ይችላል፡፡ ቀድሞም አውቀው ሊሆን ይችላል ፤ እርሱ ጉዳት ውስጥ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ እኔ በብቃት ነው ስለማምን ይሆነኘል ብዬ ነው የመረጥኩት፡፡ አሁን የጉዳት ችግር የለብኝም ካለ በግልፅ ሀሳቡን ማስቀመጥ አለበት ”

 

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *