የኢትዮጵያ ብሄረራዊ ቡድን ለ2017 የአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ወደ ሌሶቶ ተጉዞ ጌታነህ ከበደ ባስቆጠራቸው ሁለት ግሩም ግቦች አሸንፎ ተመልሷል፡፡ ብሄራዊ ቡድኑን በጊዜያዊነት የተረከቡት አሰልጣኝ ገብረመድህን ኃይሌም በመጀመርያ ጨዋታቸው ድል ቀንቷቸዋል፡፡
ብሄራዊ ቡድኑ ዛሬ ምሽት ቦሌ አየር ማረፍያ ሲደርስ አሰልጣኝ ገብረመድህን ከሶከር ኢትዮጵያ ጋር ቆይታ አድርገዋል፡፡
በመጀመርያ ጨዋታ ድል
” እጅግ በጣም ደስ ይላል ፤ ኩራት ነው የሚሰማኝ፡፡ ለኔ በመጀመርያ ጨዋታዬ ፣ ጨዋታው ከሜዳ ውጪ በሆነበት እና ውጤት ባጣንበት ጊዜ የተመዘገበ በመሆኑ ደስታ ተሰምቶኛል፡፡ ”
የመጀመርያው አጋማሽ
መልካም ነበር፡፡ በተለይ የመጀመርያ 45 ደቂቃ ላይ ይዘነው የገባነው እቅድ በማጥቃት ላይ መሰረት ያደረገ ስለነበር ብዙ የግብ እድሎችን ፈጥረናል፡፡ ሆኖም ማግባት አልቻልንም ነበር፡፡ በመጨረሻ እረፍት ልንወጣ ስንል ጎል ማስቆጠራችን ትልቅ ሞራል ሰጥቶናል
የ2ኛው አጋማሽ ውጥረት…
” በሁለተኛው አጋማሽ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ ሁለተኛ ግብ አስቆጥረናል፡፡ ከዛ በኋላ ያው ውጤት ለመጠበቅ ከነበረን ፍላጎት የተነሳ የተወሰነ ጫና ተፈጥሮብናል፡፡ ”
የጨዋታ ፍላጎት እና ተነሳሽነት
” በመጀመርያ በምን መልኩ መጫወት እንዳለባቸው ማስረዳት ፣ ማነሳሳት እና አንድነት እንዲፈጥሩ ማድረግ … ታክቲኩ እንዳለ ሆኖ እነዚህ ነገሮች ተደምረው ነው በሙሉ ፍላጎት እንዲጫወቱ ያደረጋቸው፡፡”
ስለ ተጫዋቾቹ
” እኔ ከመጀመርያው ምን አይነት ውጤት ሊመዘገብ እንደሚችል ከጨዋታ በፊት ነግሬያቹ ነበር፡፡ የነበራቸው ተነሳሽነት ፣ የስራ ፍላጎታቸው ፣ ለኔ የነበራቸው ስሜት ጥሩ ስለነበር ይቀበሉኝ ነበር፡፡ በትክክል ውጤትም ይመዘገብ እንደነበር ያስታውቅ ነበር። ”
የማለፍ ተስፋ
” የማለፍ እድላችን በእኛ ላይ ብቻ የተመሰረተ አይደለም፡፡ በሌሎች ምድቦች ውጤት ጭምር ስለሆነ ቀጣይ ያለው ነገር የሚታይ ነው የሚሆነው፡፡ ዋናው እኛ ያለንን ቀሪ አንድ ጨዋታ አሸንፈን የቤት ስራችንን መጨረስ ነው”
በስታድየም ስለነበሩ ደጋፊዎች
” በእውነት ከፍተኛ የሆነ ክብር አለኝ፡፡ በጣም ብዙ ነበሩ፡፡ ኢትዮዽያዊነት በጣም ደስ ይላል ፤ ሁልጊዜ ከጎንህ ይቆማሉ ፣ ማልያ ለብሰው ሜዳ በመምጣት ሆቴል ድረስ ያላቸውን ፍቅር ሲገልፁ ደስ ይላሉ ”