ቅዱስ ጊዮርጊስ በመጨረሻ ደቂቃ ነጥብ ሲጋራ ሁለተኛው ወራጅ ክለብ አሁንም አለየለትም

የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ 25ኛ ሳምንት ሁሉም ጨዋታዎች ዛሬ ሲካሄዱ ሻምፒዮኑ ቅዱስ ጊዮርጊስ ነጥብ ጥሏል፡፡ በዳሽን እና ኤሌክትሪክ መካከል ላለመውረድ የሚደረገው ፍጥጫም እስከመጨረሻው ሳምንት ዘልቋል፡፡

09:00 ላይ አዳማ ከተማን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካለግብ ነጥብ ተጋርቶ ወጥቷል፡፡ ጨዋታው የተቀዛቀዘና እጅግ ጥቂት የግብ እድሎች የተፈጠሩበት ሆኖ ተጠናቋል፡፡

ወደ ድሬዳዋ ያቀናው ደደቢት 2-1 አሸንፏል፡፡ ደደቢት በዳዊት ፍቃዱ ግብ ቀዳሚ መሆን ሲችል በላይ አባይነህ ባለሜዳዎቹን አቻ ማድረግ ችሎ ነበር፡፡ የሰማያዊዎቹን የድል  ግብ ከመረብ ያሳረፈው ናይጄርዊው ሳሙኤል ሳኑሚ ነው፡፡

ወደ ሆሳዕና ያቀናው ኢትዮጽያ ቡና ወራጁ  ሀዲያ ሆሳዕናን 2-1 አሸንፏል፡፡ ያቡን ዊልያም እና ሳዲቅ ሴቾ የቡናን የድል ግብ ከመረብ ሲያሳርፍ ዱላ ሙላቱ የሀዲያ ሆሳዕናን ግብ ከመረብ አሳርፏል፡፡

ወደ ይርጋለም የተጓዘው አርባምንጭ ከተማ ካለ ግብ አቻ ተለያይቷል፡፡ ይህ ውጤት ለአርባምንጭ ከተማ ከመውረድ ስጋት ነጻ ያወጣ ሆኖ ተመዝግቧል፡፡

ኤሌክትሪክ ከቦዲቲ 1 ነጥብ ይዞ ተመልሷል፡፡ ወላይታ ድቻን የገጠመው ኤሌክትሪክ ካለ ግብ 0-0 ማጠናቀቁን ተከትሎ ከዳሽን ጋር ያለው የነጥብ ልዩነቱን ማስጠበቅ ችሏል፡፡

PicsArt_1466791221596

ሀዋሳ ላይ ሀዋሳ ከተማ ዳሽን ቢራን አስተናግዶ 2-2 ተለያይቷል፡፡ ሀዋሳ ከተማዎች በዮሃንስ ሰገቦ እና ፍርድአወቅ ሲሳይ ግቦች 2-0 ሲመሩ ቆይተው ኤዶም ሆሶዎሮቪ እና የተሻ ግዛው የጎንደሩን ክለብ አቻ አድርገዋል፡፡

በጨዋታው ጫማውን ለመስቀል ከውሳኔ ላይ የደረሰው ሙሉጌታ ምህረት ከደጋፊዎች ስጦታ የተበረከተለት ሲሆን ፍርዳወቅ ሲሳይ ግብ ካስቆጠረ በኋላ ለሙሉጌታ ያለውን ክብር ገልጿል፡፡

PicsArt_1466791177955

ውጤቱ ዳሽን ቢራ በወራጅ ቀጠናው ውስጥ እንዲቆይ ያስገደደው ሲሆን የመጨረሻውን ጨዋታ አሸንፎ የኤሌክትሪክን ውጤት የመጠበቅ ግዴታ ውስጥ ገብቷል፡፡

11:30 ላይ ሻምፒዮኑ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከመከላከያ ጋር አቻ ተለያይቷል፡፡ በጨዋታው መጀመርያ የመከላከያ ተጫዋቾች የቅዱስ ጊዮርጊስ ተጫዋቾችን በክብር በማጀብ ወደ ሜዳ ገብተዋል፡፡

መሃመድ ናስር በ9ኛው ደቂቃ የኦዶንካራን ስህተት ተጠቅሞ ባስቆጠረው ግብ መከላከያ እስከ ጨዋታው መገባደጃ ድረስ መምራት ቢችልም ተቀይሮ የገባው ዳዋ ሁቴሳ በ90+4ኛው ደቂቃ ቅዱስ ጊዮርጊስን ከሽንፈት የታደገች ግብ ከመረብ አሳርፏል፡፡

ግቧ የተቆጠረችው የተጨመረው ደቂቃ ካለፈ በኋላ ነው በሚል የመከላከያ ቡድን አባላት ከዳኞች ጋር ውዝግብ ሲፈጥሩ ታይቷል፡፡

PicsArt_1466791469826

ሊጉ በመጪው ማክሰኞ እና ረቡዕ በሚደረጉ ጨዋታዎች ፍፃሜውን ያገኛል፡፡ ሻምፒዮኑ እና አንደኛው ወራጅ ቡድን ቀደም ብለው በመታወቃቸው በመጨመረሻው ሳምንት ጨዋታዎች የሚጠበቀው ሀዲያ ሆሳዕናን ተከትሎ ማን ወደ ከፍተኛ ሊግ ይወርዳል የሚለው ይሆናል፡፡ ዳሽን 25 ፣ ኤሌክትሪክ 27 ነጥብ ይዘው ላለመውረድ ተፋጠዋል፡፡

PicsArt_1466791341761

ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪነቱን ታፈሰ ተስፋዬ በ14 ግቦች ሲመራ ዳዊት ፍቃዱ በ12 ይከተላል፡፡

PicsArt_1466791405455

የ26ኛ ሳምንት ጨዋታዎች

ማክሰኞ ሰኔ 21 ቀን 2008

08፡00 ዳሽን ቢራ ከ ሲዳማ ቡና (አዳማ)

09፡00 ኤሌክትሪክ ከ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ (አበበ ቢቂላ ስታድየም)

09፡00 አርባምንጭ ከተማ ከ ድሬዳዋ ከተማ (አርባምንጭ)

10፡00 አዳማ ከተማ ከ መከላከያ (አዳማ)

11፡30 ኢትዮጵያ ቡና ከ ወላይታ ድቻ (አአ ስታድየም)

ረቡዕ ሰኔ 22 ቀን 2008

08፡30 ደደቢት ከ ሀዲያ ሆሳዕና (አአ ስታድየም)

10፡30 ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ ሀዋሳ ከተማ (አአ ስታድየም)

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *