የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ የመጨረሻ ሳምንት ዛሬ በተደረጉ 5 ጨዋታዎች ሲጀምር ኤሌክትሪክ ከመውረድ የተረፈበትን ውጤት አስመዝግቧል፡፡ ኢትዮጵያ ቡና በ2ኝነት ሲያጠናቅቅ ዳሽን ቢራ ወደ ከፍተኛ ሊግ ወርዷል፡፡
በተመሳሳይ 08:00 ጨዋታቸውን ያደረጉት ኤሌክትሪክ እና ዳሽን ቢራ ተጋጣሚዎቻቸውን ቢያሸንፉም በእለቱ ደስተኛ ለመሆን የታደለው ኤሌክትሪክ ሆኗል፡፡
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክን የገጠመው ኤሌክትሪክ 1-0 አሸንፏል፡፡ የቀዮቹን የአመቱ ወሳኝ ግብ ከመረብ ያሳረፈው ፒተር ኑዋዲኬ ነው፡፡ ድሉ ኤሌክትሪክ ነጥቡን 30 አድርሶ ለከርሞ በሊጉ መቆየቱን እንዲያረጋግጥ ረድቶታል፡፡
አዳማ ላይ ሲዳማ ቡናን ያስተናገደው ዳሽን ቢራ 1-0 ቢያሸንፍም ከመውረድ መትረፍ አልቻለም፡፡ የዳሽንን ብቸኛ ግብ ከመረብ ያሳረፈው ኤዶም ሆሶውሮቪ ነው፡፡ 28 ነጥቦች የሰበሰበው ዳሽን ቢራ በ2006 ካደገበት ፕሪሚየር ሊግ መሰናበቱን አረጋግጧል፡፡
09:00 ላይ ድሬዳዋ ከተማን ያስተናገደው አርባምንጭ ከተማ 4-1 በማሸነፍ የውድድር ዘመኑን በድል አጠናቋል፡፡ የአርባምንጭን የድል ግቦች ተሾመ ታደሰ ፣ አመለ ሚልኪያስ ፣ አማኑኤል ጎበና እና ታደለ መንገሻ ሲያስቆጥሩ በላይ አባይነህ የድሬዳዋ ከተማን ግብ አስቆጥሯል፡፡
በአንደኛው ዙር እጅግ ደካማ የነበረው አርባምንጭ የቤት ስራውን በሚገባ ሰርቶ አጨራረሱን ሲያሳምር ጥሩ ደረጃ ላይ የነበረው ድሬዳዋ በአስደንጋጭ ሁኔታ አሽቆልቁሎ ከወራጅ ቀጠናው ለጥቂት ተርፏል፡፡
10:00 ላይ በአበበ ቢቂላ ዝግ ስታድየም ወላይታ ድቻን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ቡና 1-0 አሸንፎ የውድድር ዘመኑን በ2ኝነት አጠናቋል፡፡ የቡናን ብቸኛ የድል ግብ ከመረብ ያሳረፈው ጋቶች ፓኖም ነው፡፡ አዳማ ከተማ ነጥብ መጣሉን ተከትሎ ኢትዮጵያ ቡና 2ኛ ደረጃ ተቀምጦ መጨረስ ችሏል፡፡
አዳማ ላይ መከላከያን ያስተናገደው አዳማ ከተማ 1-1 ተለያይቶ 2ኛ ደረጃ ይዞ ለመጨረስ የነበረውን እድል አምክኗል፡፡
በአዲስ ማልያ እና ባነር በያዙ ደጋፊዎች በደመቀው ጨዋታ በርካታ ካርድ የታየ ሲሆን ከዕረፍት በኃላ ምንተስኖት ከበደ በቀጥታ ቀይ ካርድ ከሜዳ ተሰናብቷል፡፡
አዳማ ታፈሰ ተስፋዬ የግል ጥረቱን ተጠቅሞ ባስቆጠረው ግብ ቀዳሚ ሲሆን ባዬ ገዛኸኝ መከላከያን አቻ አድርጓል፡፡
የሊጉ የመጨረሻ ሁለት ጨዋታዎች ነገ ሲካሄዱ ደደቢት ሀዲያ ሆሳዕናን 08:30 ላይ ያስተናግዳል፡፡ ቻምፒዮኑ ቅዱስ ጊዮርጊስ ደግሞ 10:30 ላይ ሀዋሳ ከተማን ይገጥማል፡፡
የደረጃ ሰንጠረዥ
ከፍተኛ ግብ አግቢዎች