የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ክለቦች ጥሎ ማለፍ (ሊግ ዋንጫ) ዛሬ ፍጻሜውን ሲያገኝ ቅዱስ ጊዮርጊስ በመለያ ሞቶች መከላከያን በማሸነፍ ቻምፒዮን ሆኗል፡፡ የውድድር ዘመኑንም በሁለትዮሽ አሸናፊነት አጠናቋል፡፡
09:20 በተጀመረው ጨዋታ ሁለቱም ቡድኖች በግማሽ ፍፃሜው የተጠቀሙበትን አሰላለፍ ቡድን ሙሉ ለሙሉ የተጠቀሙ ሲሆን የመጀመርያው አጋማሽ ፈጣን እንቅስቃሴ እና በርካታ የማስጠንቀቂያ ካርዶች የታዩበት ነበር፡፡
በ14ኛው ደቂቃ ሳሙኤል ሳሊሶ ከቅጣት ምት በቀጥታ ግሩም ግብ አስቆጥሮ መከላከያን ቀዳሚ ማድረግ የቻለ ሲሆን ጦረኞቹ ተጨማሪ ግቦች ለማስቆጠር ያደረጉት ጥረት በግብ ጠባቂው ዘሪሁን ታደለ ከሽፈዋል፡፡
የመከላከያ ፈጣን እንቅስቃሴ ለቅዱስ ጊዮርጊሶች ፈታኝ የነበረ ሲሆን ጥፋቶቸች በመስራት በርካታ የማስጠንቀቂያ ካርዶች እንዲመለከቱ አስገድዷቸዋል፡፡
ከእረፍት መልስ የተሻለ እንቅስቃሴ ማድረግ የቻሉት ቅዱስ ጊዮርጊሶች በ57ኛው በፍጹም ቅጣት ምት ክልል ውስጥ ኳስ በእጅ በመነካቱ የተሰጠውን የፍጹም ቅጣት ምት አዳነ ግርማ ወደ ግብነት ቀይሮ አቻ ሆነዋል፡፡ ከአቻነት ግቡ በኀላ አንድ ጊዜ ሞቅ አንድ ጊዜ ቀዝቀዝ እያለ ተመጣጣኝ እንቅስቃሴ አስተናግዶ ጨዋታው ከመጠናቀቁ በፊት የፕሪሚየር ሊጉ ኮከብ ተጫዋች አስቻለው ታመነ በ2ኛ ቢጫ ከሜዳ ተወግዷል፡፡
ከሁለቱም ቡድኖች በኩል የመለያ ምቶች ላይ ለመጠቀም በሚመስል መልኩ የተጫዋች ለውጦች ተደርገው መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ 1-1 ተጠናቋል፡፡
በተሰጡት የመለያ ምቶች የቅዱስ ጊዮርጊስ ተጫዋቾች በሙሉ ሲያስቆጥሩ ከመከላከያ ቴዎድሮስ ታፈሰ እና ቴዎድሮስ በቀለ የመቷቸው ኳሶችን ዘሪሁን ታደለ መልሷቸው የእለቱ ጀግና መሆን ችሏል፡፡ ቅዱስ ጊዮርጊስም በመለያ ምቶች 4-3 በማሸነፍ የዋንጫው ባለቤት ሆኗል፡፡
በጨዋታው መጨረሻ ተቀይረው ከገቡት መካከል አበባው ቡታቆ እና በሃይሉ ግርማ ሲያስቆጥሩ ቴዎድሮስ ታፈሰ ስቷል፡፡ ግብ ጠባቂው ይድነቃቸው ኪዳኔ ደግሞ ምንም ኳስ ማዳን ሳይችል ቀርቷል፡፡
ቅዱስ ጊዮርጊስ የጥሎ ማለፉን ቻምፒዮን መሆኑን ተከትሎ የውድድር ዘመኑን በሁለትዮሽ ዋንጫ ማጠናቀቅ የቻለ ሲሆን 2008 ከገባ በኀላ ደግሞ 3ኛ ዋንጫውን አንስቷል፡፡
ከ2001 በኋላ የሁለትዮሽ ዋንጫ ማሳካት የቻለው ቅዱስ ጊዮርጊስ የጥሎ ማለፉን ዋንጫ ሲያነሳ በታሪክ ለ11ኛ ጊዜ ነው፡፡