የሀምሌ 1 አጫጭር ዜናዎች እና ጥቆማዎች

አሰልጣኝ ድራጋን ፖፓዲች በኢትዮጵያ ቡና አይቀጥሉም 

አሰልጣኝ ድራጋን ፖፓዲች ለከርሞ ከኢትዮጵያ ቡና ጋር እንደማይቀጥሉ ታውቋል፡፡ ቡና ሰርቢያዊውን አሰልጣኝ በክብር ለመሸኘት ያሰበ ሲሆን ለቀጣዩ አመትም ፊቱን ወደ ሀገር ውስጥ አሰልጣኞች እንደሚያዞር ተነግሯል፡፡ በቀጣዮቹ ቀናትም አዲሱ አሰልጣኝ ይፋ ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡


PicsArt_1467996790035

ቅዱስ ጊዮርጊስ ፍሬው ሰለሞን እና ታደለ መንገሻ ላይ አነጣጥሯል

ቅዱስ ጊዮርጊስ ታደለ መንገሻና ፍሬው ሰለሞንን የግሉ ለማድረግ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ተሰምቷል፡፡ ክለቡ በክረምቱ የፈጣሪ አማካይ ችግሩን ለመቅረፍ ቆድሚያ እንደሚሰጥ ታውቋል፡፡ ፍሬው የመከላከያ ኮንትራቱ የተጠናቀቀ ሲሆን ታደለ ወደ አርባምንጭ ያመራው በአንድ አመት ኮንትራት እንደነበር የሚታወስ ነው፡፡


ገብረመድህን ሃይሌ ወደ ኤሌክትሪክ?

ከመከላከያ ጋር በስምምነት መለያየታቸውን ትላንት ይፋ ያደረጉት አሰልጣኝ ገብረመድህን ኃይሌ ወደ ኤሌክትሪክ ለማምራት መቃረባቸው ተነግሯል፡፡ አሰልጣኙ ከኢትዮጵያ ቡና ጋርም ስማቸው ተያይዟል፡፡


PicsArt_1467996887003

አስራት መገርሳ እና ሳሚ ሳኑሚ በኢትዮጵያ ቡና ተፈልገዋል

ኢትዮጵያ ቡና አስራት መገርሳ እና ሳሙኤል ሳኑሚ ከኢትዮዽያ ቡና ጋር ስማቸው ተያይዞ እየተነሳ ይገኛል፡፡ አስራት ከዳሽን ጋር ቀሪ የአንድ አመት ኮንትራት የሚቀረው ቢሆንም የዳሽን ወደ ከፍተኛ ሊግ መውረድ ለቡና መልካም አጋጣሚ ነው ተብሏል፡፡


መከላከያ ምንያምር ጸጋዬን ዋና አሰልጣኝ ለማድረግ አስቧል

መከላከያ ከአሰልጣኝ ገብረመድህን ኃይሌ ጋር ከተለያየ በኋላ አዲስ አሰልጣኝ ፍለጋ ወደ ገብያ ላይወጣ እንደሚችል ተነግሯል፡፡

መከላከያ ቦታውን የገብረመድህን ረዳት ሆነው ሲሰሩ የነበሩት መቶ አለቃ ምንያምር ጸጋዬን የዋና አሰልጣነት እድል ለመስጠት መወሰናቸው ተሰምቷል፡፡


PicsArt_1467996840662

አሰልጣኝ ውበቱ በሀዋሳ ከተማ ይቆያሉ

ስማቸው ከተለያዩ የአአ ክለቦች ጋር ተያይዞ ሲነሳ የነበረው አሰልጣኝ ውበቱ አባተ በሀዋሳ የመቆየታቸው ነገር እርግጥ የሆነ ይመስላል፡፡ ውበቱ በክለቡ ለመቆየት የሚያስችላቸውን ድርድር እንደጨረሱ ረዳቶቻቸውን የሚያሳውቁ ሲሆን ጫማውን የሰቀለው ሙልጌታ ምህረት የውበቱ ረዳት አሰልጣኝ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡


አሸናፊ በቀለ በአዳማ ይቆያሉ

አሰልጣኝ አሸናፊ በቀለ ከአዳማ ከተማ ጋር በቀጣዩ አመትም ለመቀጠል ከስምምነት ደርሰዋል፡፡

በውድድር ዘመኑ አጋማሽ ከክለቡ ሊሌናበቱ ጫፍ ደርሰው የነበሩት አሰልጣኝ አሸናፊ ለከርሞ ከተለያዩ ክለቦች ጋር ስማቸው ቢያያዝም በአዳማ ለመሰንበት ወስነዋል፡፡


PicsArt_1467997020104

ሲዳማ ቡና አለማየሁ አባይነህን ዋና አሰልጣኝ አድርጎ ለመቅጠር ተስማምቷል

ሲዳማ ቡና ረዳት አሰልጣኙ አለማየሁ አባይነህን ዋና አሰልጣኝ አድርጎ ለመቅጠር ከስምምነት ላይ እንደደረሱ ተሰምቷል፡፡ አሰልጣኝ አለማየሁ በውድድር ዘመኑ መጨረሻ የአርባምንጭ አሰልጣኝነታቸውን ለቀው ለቀው ሲዳማ ቡናን በረዳት አሰልጣኝነት ከተቀላቀሉ በኋላ በመጨረሻዎቹ የፕሪሚየር ሊግ ጨዋታዎች በጊዜያዊ አሰልጣኝነት ቡድኑን መርተዋል፡፡


የወሎ ኮምቦልቻ እና የአማራ ውሃ ስራ ጨዋታ ወደ ሌላ ቀን ተዘዋወረ

በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ትላንት ሲካሄድ የነበረው የወሎ ኮምቦልቻ እና አማራ ውሃ ስራ ጨዋታ ሜዳው ጨቅይቶ ለመጫወት አስቸጋሪ ሁኔታ ላይ በመገኘቱ በ75ኛው ደቂቃ ተቋርጦ ዛሬ እንዲቀጥል መወሰኑ የሚታወስ ነው፡፡ ነገር ግን ሜዳው እስካሁን አለመድረቁና ዝናብ እየመጣ ከመሆኑ አንፃር ለሌላ ጊዜ እንዲሸጋገር ተወስኗል፡፡


ከ17 አመት በታች ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ ነገ ይካሄዳል

በኢትዮጵያ ከ17 አመት በታች ዋንጫ ነገ አበበ በቂላ ስታድየም ላይ የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች ይካሄዳሉ፡፡ 07:00 ላይ ኢትዮዽያ ቡና ከ ወላይታ ድቻ ሲጫወቱ 09:00 ላይ አፍሮ ፅዮን ከ ሀዋሳ ከተማ ይጫወታሉ፡፡


የብሄራዊ ሊግ ማጠቃልያ ውድድር ባቱ ከተማ ላይ ሊካሄድ ይችላል

የኢትየጵያ ብሄራዊ ሊግ ማጠቃለያ ውድድር ከሀምሌ 14 እስከ ነሀሴ 2 እንደሚደረግ ታውቋል፡፡ የውድድሩ ስፍራም ባቱ (ዝዋይ) ከተማ ሊደረግ ይችላል ተብሏል፡፡


ከ17 አመት በታች ብሄራዊ ቡድን ለዝግጅት ሀዋሳ ከትሟል

ከ17 አመት በታች የኢትዮዽያ ብሄራዊ ቡድን ለዝግጅት ሀዋሳ ከተማ ገብቷል፡፡ ማረፊያውን ሴንትራል ሆቴል ያደረገ ሲሆን ከግብፅ ጋር እስከሚያደርገው የማጣርያ ጨዋታ መቃረቢያ ድረስ በዛው ቆይታ የሚያደርግ ያደርጋል፡፡

በአሰልጣኝ አጥናፉ የሚመራው ከ17  አመት በታች ቡድኑ ከነገ ጠዋት ጀምሮ በግብርና ሜዳ ዝግጅቱን ማድረግ እንደሚጀምር ለማወቅ ተችሏል፡፡


የክልል ክለቦች ሻምፒዮና ነሀሴ 6 ይደረጋል

ወደ ብሄራዊ ሊግ ለማለፍ የሚደረገው የኢትዮጵያ ክልል ክለቦች ሻምፒዮና ነሀሴ 6 እንደሚጀምር ተነግሯል፡፡ በ44 ቡድኖች መካከል የሚደረገው ውድድር አርባምንጭ ከተማ ላይ እንዲደረግ ታስቦ የነበረ ቢሆንም ሊቀየር ይችላል ተብሏል፡፡ በውድድሩ ሩብ ፍጻሜውን የሚቀላቀሉ 8 ክለቦች ወደ ብሄራዊ ሊግ ያልፋሉ፡፡


Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *