የ2008 የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ ቻምፒዮኑ ደደቢት አዳዲስ ተጫዋቾችን በማስፈረም እና ወሳኝ ተጫዋቾቹን በማጣት መሃል ይገኛል፡፡
ደደቢት የቅዱስ ጊዮርጊሷን አማካይ ትዕግስት ዘውዴን ሲያስፈርም የ2 ተጫዋቾቹን ኮንትራት ለተጨማሪ 2 አመታት አድሷል፡፡
የመስመር አማካይዋ ትዕግስት የሴቶች እግርኳስ የወደፊቷ ኮከብ እንደምትሆን ያሳየ ድንቅ አመት አሳልፋለች፡፡
ከአዲስ ፈራሚዋ ትዕግስት በተጨማሪ ደደቢት ሊለቁበት በሚችሉ ተጫዋቾች ምትክ ተከላካይዋ ትዕግስት ዳዊትን ከሀዋሳ ከተማ እንዲሁም ሄለን ሰይፉን ከቅዱስ ጊዮርጊስ ለማስፈረም ያሰበ ሲሆን የንግድ ባንኳ አማካይ ብሩክታዊት ግርማም ለክለቡ ሳትፈርም እንዳልቀረች ተነግሯል፡፡
ሰማያዊዎቹ ከግዢ በተጨማሪ ውላቸው የተጠናቀቀው አልፊያ ጃርሶ እና ሰናይት ባሩዳን ኮንትራት ያራዘመ ቢሆንም የመስከረም ካንኮ ፣ ሎዛ አበራ እና ሰናይት ቦጋለ እስካሁን አለመፈረም ግን ለክለቡ ስጋትን ፈጥሯል፡፡
ሶስቱ ተጫዋቾች በክለቡ በቀረበላቸው የውል ማደሻ ሂሳብ ያልተሰማሙ ሲሆን ወደ ንግድ ባንክ በከፍተኛ ሂሳብ ለማምራት መቃረባቸውም ተሰምቷል፡፡
የደደቢት ግዢ እና ኢላማዎችም የተጫዋቾቹ መልቀቅ አይቀሬ መሆኑን የሚያሳይ መስሏል፡፡