የኢትዮጵያ ከ17 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ 3ኛ ቀኑን ይዟል፡፡ ዛሬ በተደረጉ ጨዋታዎችም አዳማ ከተማ ሲያሸንፍ ወላይታ ድቻ ከመከላከያ ነጥብ ተጋርተዋል፡፡
08:00 ላይ አዳማ ከተማ ደደቢትን 2-1 በማሸነፍ ወደ ግማሽ ፍጻሜው አንድ እግሩን አስገብቷል፡፡ የአዳማን ሁለት የድል ጎሎች የኀላሸት ፍቃዱ ሲያስቆጥር ደደቢትን ከመሸነፍ ያላደነች ብቸኘ ጎል ከማል አቶም አስቆጥሯል፡፡
አዳማዎች ከዕረፍት በፊት ባስቆጠሩት ጎል ጨዋታውን ሲጨርሱ ከዕረፍት መልስ ደደቢት ወደ ጨዋታው ለመመለስ ጥረት ቢያደርግም ሳይሳካላቸው ቀርቷል፡፡
ውጤቱን ተከትሎ አዳማ ሁለቱንም ጨዋታ በማሸነፍ የምድቡ መሪ በመሆን ወደ ግማሽ ፍፃሜ የማለፍ ተስፋውን ሲያለመልም በአንፃሩ ደደቢት 1 ነጥብ ብቻ በመያዝ ወደ ግማሽ ፍፃሜ ለማለፍ ያለውን እድል አጣብቂኝ ውስጥ ከቶታል፡፡
10:00 ላይ ተመጣጣኝ እንቅስቃሴ በታየበት ፣ ተመልካቹን ቁጭ ብድግ ባደረገውና በርካታ ጎሎች በተስተናገደበት ጨዋታ ወላይታ ድቻ ከ መከላከያ 3-3 በሆነ አቻ ውጤት ተለያይተዋል፡፡
ለወላይታ ድቻ ዮናታን አስራት ፣ በረከት ወልዴ እና ሲሳይ ማሞ ሲያስቆጥሩ ለመከላከያ ዮሐንስ ደረጄ (2) እና አቤል ነጋሽ አስቆጥረዋል፡፡
በጨዋታው ላይ መልካም እንቅስቃሴ በማድረግ ከተመልካቹ አድናቆት ያገኘው የመከላከያው ዮሐንስ ደረጄ ባጋጠመው ከፍተኛ ጉዳት በፍጥነት ህክምና ለማግኘት በአንቡላስ ወደ ህክምና ጣቢያ ተወስዷል፡፡
ውድድሩ ነገ ሲቀጥል በምድብ ሀ 08:00 ላይ ሲዳማ ቡና ከ አአ ከተማ ፤ 10:00 ላይ ሀዋሳ ከተማ ከ ሐረር ሲቲ ይጫወታሉ፡፡