የኢትዮጵያ ከ17 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ የማጠቃለያ ውድድር የምድብ ጨዋታዎች ወደ መጠናቀቂያው ተቃርቧል፡፡ ዛሬ በተደረጉ የምድብ ለ የመጨረሻ ጨዋታዎችም መከላከያ ወደ ግማሽ ፍጻሜው መሸጋገሩን ያረጋገጠበት ውጤት አስመዝግቧል፡፡
04:00 ወንጂ ሜዳ ላይ ወላይታ ድቻ አዳማ ከተማን ገጥሞ 1-0 አሸንፏል፡፡ የወላይታ ድቻን ብቸኛ የድል ግብ በረከት ወንድም ከመረብ አሳርፏል፡፡
በተመሳሳይ ሰአት አዳማ አበበ ቢቂላ ላይ መከላከያ ከ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ጨዋታቸውን ካለ ግብ ፈፅመዋል፡፡
የዛሬ ውጤቶችን ተከትሎ መከላከያ እና ወላይታ ድቻ በነጥብ ፣ የግብ ልዩነት እና የግብ መጠን እኩል በመሆናቸው በውድድሩ ደንብ መሰረት ወደ ግማሽ ፍጻሜው የሚያልፈውን ክለብ ለመለየት በወጣው እጣ መከላከያ ግማሽ ፍጻሜውን ተቀላቅሏል፡፡
ውድድሩ ነገ ሲቀጥል በምድብ ሀ የመጨረሻ ጨዋታዎች በተመሳሳይ 09:00 ላይ ሐረር ሲቲ ከ ሲዳማ ቡና (ወንጂ ሜዳ) ፣ አዲስ አበባ ከተማ ከ ቅዱስ ጊዮርጊስ (አዳማ አበበ በቂላ) ይጫወታሉ፡፡
በተያያዘ ዜና የኢትዮጵያ ከ17 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ ክለቦች ጥሎ ማለፍ ፍጻሜ ቦዲቲ ስታድየም ላይ እንዲደረግ ተወስኗል፡፡
ሀዋሳ ከተማ ከ ወላይታ ድቻ ሐምሌ 30 ቀን 2008 የሚያደርጉት ጨዋታ የሚከናወንበትን ሜዳ ለመለየት በተጣለው እጣ መሰረት እድሉ ወደ ወላይታ ድቻ አምርቷል፡፡