ትላንት የተጀመረው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ሊግ የማጠቃለያ ውድድር ዛሬ በተካሄዱ 3 ጨዋታዎች ሲቀጥል አራዳ ክፍለ ከተማ እና ዲላ ከተማ ድል ቀንቷቸዋል፡፡
08:00 ላይ በባቱ ከተማ ሜዳ በአማራ ፖሊስ እና በሞጆ ከተማ መካከል የተካሄደው የምድብ ሀ ጨዋታ ያለግብ በአቻ ውጤት ተጠናቋል፡፡
በተመሳሳይ 08:00 በሼር ሜዳ በምድብ ለ የሚገኘው ዲላ ከተማ ሚዛን አማንን 1-0 አሸንፏል፡፡ በጨዋታው ላይ መልካም እንቅስቃሴ ሲያደርግ የነበረው በድሉ ዮሃንስ የዲላ ከተማን ብቸኛ የማሸነፍያ ጎል ከመረብ አሳርፏል፡፡
10:00 ላይ በሼር ሜዳ ከምድብ ለ በተደረገው ሌላ ጨዋታ አራዳ ክ/ከተማ ቡታጅራን በሰፊ የግብ ልዩነት አሸንፏል፡፡
በአራዳ ፍፁም የጨዋታ የበላይነት 4-0 በተጠናቀቀው ጨዋታ የድል ጎሎቹን አማኑኤል አዳነ ፣ አብዱልጠፍ ሙራድ እና ተቀይሮ የገባው ዮናስ በዔና (2) አስቆጥረዋል፡፡ ውጤቱ ለአራዳ ክ/ ከተማ ድንቅ አጀማመር ሲሆንለት 48 ኪ/ሜ አቋርጠው የመጡት በርካታ የቡታጅራ ደጋፊዎችን አንገት አስደፍቷል፡፡
ውድድሩ ነገ ሲቀጥል ከምድብ ሐ 08:00 መተሀራ ስኳር ከ አምበሪቾ 10:00 ላይ ካፋ ቡና ከ ከወሊሶ ከተማ በባቱ ከተማ ሜዳ ይጫወታሉ፡፡
የምድብ መ ጨዋታዎች በሼር ሜዳ ሲካሄዱ 08:00 ሶሎዳ አደዋ ከ ሽሬ እንደስላሴ ፣ 10:00 ላይ ለገጣፎ ከተማ ከ ዳባት ከተማ የሚጫወቱ ይሆናል፡፡