በዛሬው እለት ወደ ፕሪሚየር ሊግ ማደጉን ያረጋገጠው ጅማ አባ ቡና ከወዲሁ የፕሪሚየር ሊግ ልምድ ያላቸው ተጫዋቾችን መሰብሰብ ጀምሯል፡፡
ጅማ አባ ቡና ከ5 ተጫዋቾች ጋር በቃል ደረጃ ስምምነት ላይ መድረሱ የታወቀ ሲሆን በመጪዎቹ ቀናት በይፋ ከክለቡ ጋር ይፈራረማሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡
የመከላከያ ውሉን የጨረሰው መሃመድ ናስር ወደ ትውልድ ከተማው የሚመልሰውን ዝውውር ሲያደርግ ከመከላከያ ጋር በውል ማራዘም ላይ ከስምምነት መድረስ ያልቻለው የብሄራዊ ቡድኑ ግብ ጠባቂ ጀማል ጣሰውም አጥቂውን ተከትሎ ወደ ጅማ አምርቷል፡፡
በውድድር ዘመኑ ድንቅ አቋም ያሳየው የወላይታ ድቻው የአጥቂ አማካይ በድሉ መርዕድ ሌላው ለጅማ አባ ቡና ለመፈረም የተስማማ ተጫዋች ሲሆን የክለብ አጋሩ ኃይለየሱስ ብርሃኑም ጅማ ደጃፍ ደርሷል፡፡ ኃይለየሱስ በተከላካይ እና አማካይነት መጫወት የሚችል ተጫዋች ነው፡፡
አስከ ውድድር ዘመኑ መጨረሻ በሚቆይ ውል ኤሌክትሪክን ያገለገለው ፍጹም ገብረማርያም ሌላው ለጅማ አባ ቡና ለመፈረም የተስማማ ተጫዋች እንደሆነ ከክለቡ ያገኘነው መረጃ ቢያመለክትም በዩናይትድ ስቴትስ የእረፍት ጊዜውን እያሳለፈ የሚገኘው የቀድሞው የቅዱስ ጊዮርጊስ ኮከብ ከክለቡ ጋር ምንም አይነት ግንኙነት እንዳላደረገ ለሶከር ኢትዮጵያ ገልጿል፡፡ በቀጣዩ ሳምንት ወደ ሀገር ቤት ሲመለስ ቀጣይ ማረፊያውን እንደሚወስንን ጨምሮ ተናግሯል፡፡
ለአባ ቡና ለመፈረም ከስምምነት ከደረሱት ተጫዋቾች መካከል መስኡድ መሃመድ አንዱ ነው፡፡ መስኡድ ከቡና ጋር ያለው ኮንትራት እስካሁን ያልታደሰ ሲሆን በክለቡ ያለውን ቆይታ አጠራጣሪ ሆኗል፡፡
ጅማ አባ ቡና በዝውውር መስኮቱ ንቁ ተሳታፊ መሆን የቻለ ሲሆን በቀጣዩ የውድድር ዘመን ጠንካራ ተፎካካሪ ሆኖ ለመቅረብ ስራዎች እየሰራ እንደሆነ ከክለቡ አካባቢ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡