የኢትዮጵያ ከ17 አመት በታች ብሄራዊ ቡድን ከሰአታት በኋላ ወደ ግብፅ ያመራል

ማዳጋስካር ለምታስተናግደው የ2017 የአፍሪካ ከ17 አመት በታች ዋንጫ ለማለፍ የመጀመርያ ማጣርያውን ከግብፅ ጋር የሚያደርገው የኢትዮጵያ ከ17 አመት ብሄራዊ ቡድን ከ2 ሰአት በኋላ ወደ ግብፅ ይበራል፡፡

የልኡካን ቡድኑ ምሽት 4:45 ላይ ወደ ግብጽ ጉዞውን የሚጀምር ሲሆን ከ 5 ሰአት በረራ በኋላ ካይሮ ይደርሳሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በኢትዮጵያ ልኡካን ቡድን በኩል 20 ተጨዋቾችን ጨምሮ 5 የአሰልጣኞች ቡድን አባላት ፣ የቡድን መሪው አቶ ልውል ሰገድ በጋሻው ፣ ከፌዴሬሽን ፅህፈት ቤት አቶ መለሰ ፣ ከቴክኒክ ዲፖርትመት ዳንኤል ገ/ማርያም ወደ ካይሮ አምርተዋል፡፡

ቡድኑን በሀዋሳ ሲያዘጋጁ የከረሙት አሰልጣኝ አጥናፉ አለሙ ለሶከር ኢትዮጵያ በሰጡት አስተያየት ለጨዋታው እንደተዘጋጁ ተናግረዋል፡፡

” ከሐምሌ 1 – 24 ድረስ በሀዋሳ ዝግጅታችንን አድርገናል፡፡ በአካል ብቃት ፣ በቴክኒክ ፣ በታክቲክ እና ስነ ልቦና ጥሩ ዝግጅት አድርገናል፡፡ የኢንተርናሽናል የወዳጅነት ጨዋታ ባናገኝም አራት የወዳጅነት ጨዋታዎችን አድርገናል፡፡ የተሻለ ጥሩ እንቅስቃሴም አይተናል፡፡ ያሉትን ነገሮች ሁሉ ጨርሰን የግብጹ ጨዋታን እየተጠባበቅን እንገኛለን

” የምንሄደው የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ ነው፡፡ተጫዋቾቹ ጋር ለሀገር አንድ ነገር ለመስራት ጥሩ ስሜትና ፍላጎት አለ፡፡ እግር ኳስ የሚፈልገውን ሁሉ አድርገን እንመለሳለን” ብለዋል፡፡

አሰልጣኝ አጥናፉ አክለውም ስለተጋጣሚያቸው መረጃ እንደሰበሰቡ ተናግረዋል፡፡

” ከአልጄሪያ ፣ ሱዳን እና ጋቦን ጋር ያደረጓቸውን የወዳጅነት ጨዋታዎች በቪዲዮ አይተናል፡፡ ስለነሱ በቂ ነገር አውቀናል፡፡” ብለዋል፡፡

የኢትየጵያ እና የግብጽ ጨዋታ በመጪው ቅዳሜ በካይሮ ፔትሮ ስፖርት ስታድየም ይካሄዳል፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *