በባቱ ከተማ አስተናጋጅነት እየተካሄደ የሚገኘው የኢትዮዽያ ብሄራዊ ሊግ የማጠቃልያ ውድድር ቀጣይ የሩብ ፍጻሜ ጨዋታዎች ዛሬ ሲደረጉ ሽረ እንዳስላሴ እና ለገጣፎ ከተማ ወደ ከፍተኛ ሊጉ ማደጋቸውን ያረጋገጡበትን ድል አስመዝግበዋል፡፡
08:00 ላይ በተደረገው የመጀመርያ ጨዋታ ሽረ እንዳስላሴ መተሀራ ስኳርን 1-0 በማሸነፍ የከፍተኛ ሊግ ተሳታፊ መሆኑን አረጋግጧል፡፡ የሽረን ወሳኝ የድል ጎል ሰይድ ሁሴን ሲየስቆጥር ለውጤቱ ማማር የአንበሳውን ድርሻ በመውሰድ ትልቁን ሚና የተወጣው ግብ ጠባቂው ተክላይ በርሄ ድንቅ ሆኖ ውሏል፡፡
ከሰሜን ምዕራብ ዞን ምድብ ለ በጥሩ 3ኝነት ወደ ማጠቃለያው ያለፈው ሽረ ዞኑን በቻምፒዮንነት ያጠናቀቀው መተሃራን በመርታት ለከፍተኛ ሊግ በቅቷል፡፡
10:00 ላይ በተካሄደውና ድራማዊ ክስተት በታየበት ጨዋታ ለገጣፎ ከተማ ከፋ ቡናን በመለያ ምት 5-4 በማሸነፍ ከፍተኛ ሊግ የገባ አራተኛው ቡድን ሆኗል፡፡
መደበኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ 3-3 በተጠናቀቀበት ጨዋታ ለለገጣፎ ከተማ ልደቱ ለማ ሶስቱንም ጎል በማስቆጠር የውድድሩ የመጀመርያ ሀትሪክ ሰርቷል፡፡ ለካፋ ቡና ምንተስኖት ታረቀኝ እና አንተነህ ከበደ (2) አስቆጥረዋል፡፡
አሸናፊውን ለመለየት በተሰጠው የመለያ ምት ለገጣፎ ከተማ ከፋ ቡናን 5-4 በማሸነፍ ወልቂጤ ፣ አራዳ እና ሽረ እንዳስላሴን ተከትሎ ወደ ከፍተኛ ሊግ አድጓል፡፡
በሩብ ፍጻሜው ሽንፈት ያጋጠማቸው ዲላ ከተማ ፣ መተሃራ ስኳር ፣ አማራ ፖሊስ እና ካፋ ቡና ነገ ጠዋት በሚወጣው እጣ መሰረት ቅዳሜ እለት እርስ በእርስ በመጫወት ወደ ከፍተኛ ሊግ የማለፍ እድላቸውን በድጋሚ ይሞክራሉ፡፡ የተሳካላቸው ሁለት ክለቦችም 5ኛ እና 6ኛ ቡድን በመሆን ወደ ከፍተኛ ሊጉ ያድጋሉ፡፡
የግማሽ ፍጻሜ ጨዋታዎች
እሁድ ነሀሴ 1 ቀን 2008
ለገጣፎ ከተማ ከ ሽረ እንዳስለሴ
አራዳ ክ/ከተማ ከ ወልቂጤ ከተማ
በተያየዘ ዜና የዲሲፕሊን ኮሚቴው በወልቂጤ ከተማ ላይ የገንዘብ ቅጣት አሳልፏል፡፡
የቅጣት ውሳኔው ደብዳቤ ይህንን ይመስላል፡-