ጋቦን ለምታስተናግደው የአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ የሚደረጉ የምድብ ማጣሪያ ጨዋታዎች በነሃሴ ወር መጨረሻ ይገባደዳሉ፡፡
ለአፍሪካ ዋንጫው የማለፍ እጅግ በጣም የጠበበ ዕድል ያላት ኢትዮጵያ ሲሸልስን ሃዋሳ ላይ ታስተናግዳለች፡፡ ጨዋታው አርብ ነሃሴ 27 በ10:00 እንዲካሄድ ካፍ የወሰነ ሲሆን የጨዋታ ዳኞቹ ከዩጋንዳ እንደሆኑ ታውቋል፡፡
የምድብ 10 የመጨረሻ ጨዋታ የሚመሩት ዋና ዳኛ ብራያን ሚሮ ናሱቡጋ፣ ረዳቶቹ ማርክ ሶንኮ እና ሁሴን ቡጌምቤ ናቸው፡፡ ብሪያን ናሱባጋ በ2015 ዩጋንዳ ዋንጫ የፍፃሜ ጨዋታን በአራተኛ ዳኝነት እየመራ ጨዋታው የተቋረጠ ሲሆን የዩጋንዳ እግርኳስ ማህበር (ፉፋ) ካገዳቸው ዳኞች መካከል ነበር፡፡ እግዱ ወዲያው የተነሳለት ብሪያን ከዚህ ቀደም በ2013 የኢትዮጵያ ከ17 ዓመት በታች ብሄራዊ ቡድን ቱኒዚያን አዲስ አበባ ላይ 3-0 በ2013 ሲያሸንፍ ጨዋታውን በመሃል ዳኝነት መምራት ችሏል፡፡
ዋሊያዎቹ በሃዋሳ ከትመው ዝግጅታቸውን እያደረጉ ሲሆን የምድብ አምስተኛው መርሃ ግብር ጨዋታቸውን ሌሶቶን በጌታነህ ከበደ ሁለት ግቦች 2-1 ማሸነፉ ይታወሳል፡፡ ከምድብ አስር አልጄሪያ አስቀድማ ወደ አፍሪካ ዋንጫው ያለፈች በመሆኑ ኢትዮጵያ ጥሩ ሁለተኛ ሆኖ የማለፍ ተስፋዋ በሌሎች የምድብ ጨዋታች ውጤቶች ላይ የተመሰረተ ነው፡፡